በመሪራስ አማን በላይ ተጻፈ። ከታላቅ ምስጋና ጋር
የአፄ ይኩኖ አምላክ የልጅ ልጅ የአፄ ውድም አርእድ ልጅ አምደጽዮን ስመ መንግሥታቸውን ሣልሣዊ ገብረመስቀል (ንጉሥ ላሊበላ) ንጉሠ ነገሥት ዘኢትዮጵያ ተብለው በአንድ ሺህ ሁለት መቶ ዘጠና ስምንት (1298) ዓ.ም. ነገሡ።
የቀደማዊው ምኒልክን (ምንይልክ) ዘርና የነገሥታቱን ታሪክ ለማጥፋት ሮማውያንና አረቦች በሚልኳቸው መልእክተኞቻቸውና ጳጳሳቶች ከአዳም እስከ ምኒልክ የተጻፈው መጽሐፈ ሱባኤ መጽሐፈ አበው ከምኒሊክ እስከ አልአሜዳ ዘመን የተጻፉት መጽሐፍት ተለቅመው ጠፍተው በምትካቸው በአረብኛ ቃል የተጻፉ ተተክተው ሳለ እንዲሁ አይሁዳዊ የሆነቸው የአረቦች ጠላት ዮዲት ተነስታ የአረብኛን መጻሕፍቶችና አዋቂዎችን ስታቃጥል እንዲሁ አብሮ የነበረው በግእዝ የተጻፈው መጻሕፍ ሁሉ የሚበልጠው ተቃጥሎ ነበር።
ከግብፅ የመጡት ጳጳስ አባ ያዕቆብ፡ በአፄ አምደጽዮን መልካም ተግባር እንዲሁም የኖረውንና የተደበቀውን መጻሕፍት ሁሉ አሰባስቦ በመጻፉ ተናደዱና በየገዳማቱ በየአድባራቱ ለሚኖሩ መነኮሳትና መምህራን ጥሪ አድርገው እኛን ሳያማክር ሳይጥይቅ ወደየገዳማቱ መጻሕፍቶችን ልኮአልና እንዲቃጠሉ ምእመናኑም ለአፄ አምደጽዮን እንዳይገዙ አውግዙ ብለው የኤጲስ ቆጶስነት ማእረግ እየሰጡ ላኩዋቸው። አላማቸውም አፄ አምድጽዮን የአጻፉትን መጻሕፍት እንዳይቀበሉ ለማውገዝ ነበር።
በዚህን ጊዜ የጳጳሱን ፍቅድ ለመሙላት ብለው አባ አኖሪዎስና አባ ፊልጶስ የደብረ ሊባኖስን መነኮሳት አስከትለው ንጉሠ ነገሥቱ አፄ አምደጽዮን ከሚኖሩበት ዳጉ ሂደው በድፍረት ስር ማሽና ቅጠል በጣሽ አስማት ደጋሚ ደብተራ ሰብስበህ እግዚአብሔር የማይወደውን መጽሐፍት አጽፈህ በየገዳማቱ ልከሃልና በቶሎ ሳይራባ እንዲቃጠል አድርግ አሉት።
አፄ አምደጽዮንም እኔ የፃፍኩት እግዚአብሔር ለአባቶቻችን የአደረገላቸውን ተአምርና ቃልኪዳን እንዲሁ በዘመናቸው የሆነውን ሁሉ ለትውልድ ታሪካቸው እንዲተላለፍ እንዳይረሳ አጽፌአለሁ እንጂ እናንተ እነደምትሉትና እንደምታስወሩት አይደለም አላቸው።
አባ አኖሬዎስም ታሪክ ብትፈልግ ከግብጽ ለኛ ብለው የመጡትን ጳጳስ ቃል በሰማህና የሚሉህን ባደረክ ነበር፡ ግን አሁን በራስህ ፍላጎት ያደረከውን ስህተት አምነህ መጽሐፍቱን አሰብስብህ ባታቃጥለው አውግዤሃለሁ አገርም አይገዛልህ ብለው ተናገሩት።
ንጉሥ አምደጽዮንም አባ አኖሪዎስን በገበያ ላይ በጅራፍ እንዲገረፉ አዘዘ።
በዚህን ጊዜ የቤተ ክህነቱ ወገን በአባ አኖሬዎስ መገረፍ አጉረመረመ፡ ስሙንም ለማጥፋትና ለማቆሸሽ የአባቱን እቁባት እህቱንም አገባ ከሃዲም ነው ብለው መነኮሳቱ እየፃፉ በየገዳማቱ ላኩ አስወሩበትም፡ ነገር ግን ውግዘቱም ሆነ ሐሰተኛው ወሬ አምደጽዮንን ከክብራቸው ከመንግሥታቸው ሊያወርዳቸው ቀርቶ እንዲያውም በጦርነትም ይሁን በመንፈሳዊ ሥራቸው የእግዚአብሔር መንፈስ አልተለያቸውም፡ ከቀን ወደቀን መንግሥታቸው እየጸና እስከ ውቅያኖስ ባሕር ድረስ ባሉ ጎሣዎች ተከበሩ ታወቁ።
በአፄ አምደጽዮን መንግሥት ላይ የሚያምጽና መንግሥታቸውን የሚገለብጥ ሌላ ሰው እንዲነግሥ ቤተ ክህነቱ ተማከረ፡ በጻጻሱ በአባ ያእቆብ አሳሳቢነት በሚፈለጉበት የቱርክና የግብጽ የየመን ሱልጣኖችና ሸሆች በኢትዮጵያው በክርስቲያኑ መንግሥት ላይ እንዲያምጹና እንዲወጉት ለባላባቶች የጦር መሣርያና የጦር አሰልጣኞች ለወላስማዎች ላኩላቸው። የተላኩትም ከባላባቶች ጋር መጥተው ተቀላቀሉ።
በዚህን ጊዜ በንጉሥ አምደጽዮን በኩል ያለውን ኃይል የሚገልጽ ሰላይ እየላኩ ለይፋቱ ባላባት ለሃቅ አድዲን እንዲያምጽና እንዲዋጋ በአረብኛ ጽፈው ላኩለት። እርሱም ከአዳሉ ባላባት ጋር ተማክሮ ለአምደጽዮን እንደማይገብር አስታወቀ።
እንደዚህም ሆነ፡ ሃቅ አድዲን በወላስማ ላይ የበላይ እንደሆነ ኢትዮጵያንም ጠቅልዬ የክርስቲያን መንግሥት አጥፍቼ የእስላም መንግሥት በምትኩ አስቀምጣለሁ ብሎ ክርስቲያኖችን መግደል ዓብያተ ክርስቲያናትን ማፍረስ ጀመረ። እንዲሁም ንጉሥ ነገሥቱ እንደሚያደርጉት በኢትዮጵያ አገሮች የሚሾሙትን ሱልጣኖችና ኢማሞች ከሊፋዎችንም እየሾመ ይዘጋጅ ጀመር።
አፄ አምደጽዮንም ይህንን ወሬ በሰሙ ጊዜ በ1300 ዓ.ም ከተጉለት ወደ ይፋት ሄደው በወንድሙ በደራደርና በሐቅ አድዲን እየተመራ የሚመጣውን ሠራዊት ድል አድርገው ደራደርን በፈረሱ ላይ እንዳለ በጦር ወግተው ገደሉት። የእስላሞች ጦር መሪ ባላባት ሐቅ አድዲን ወደ ግዞት ወደ ጎጃም ተላከ። በእርሱ ፈንታ የወላስማን ማዕረግ ለወንድሙ ልጅ ለሰበን ሰጥተው የአመጸውን ሽረው ያላደመውን ሹመው በሰላም ወደ ዳጎ ተጉለት ተመለሱ።
አፄ አምደጽዮን በነገሡ በአሥራ ስምንተኛው ዘመነ መንግሥታቸው በወላስማ ስብረዲን የሚባል እስላም ተነሳና ለአምደጽዮን የሚገዛውንና የሚገብረውን ሁሉ አጥፍቶ አብያተ ክርስቲያናትን አቃጥሎ በምትኩ ጃሚዎችንና መስጊዶችን ማሰራት ክርስቲያኖችን መግደል ጀመረ።
አፄ አምደጽዮንም ሊቀ አፍራስ ዘየማን ሊቀ አፍራስ ዘጸጋም ሊቃውንተ ሃራ ዘፄዋ የሆኑትን ሁሉ ጥሪ አድርገው ከሾሙና ከሸለሙ በኋላ ሰብረዲን (ሰበር–አደዲን)ወደሚኖርበት ወደ አዳልና ወደ ሞራ አገር ላኳቸው።
ከተላኩትም የቀኝ ፈረሰኞች የግራ ፈረሰኞች የጨዋ ሠራዊት አለቆች ከሰበር አደዲን ሠራዊት ጋር ገጥመው ድል አድርገው ብዙ ህዝብ ከማረኩና የታሰሩትን ከአስፈቱ በኋላ በመንደሩ ብዙ ወርቅና የዳሉል ሉል ድንጋይ ከአረብ አገር የተላከለት የጦር መስሪያ ሰይፍና ጦር ከሰብር አደዲን ቤት አግኝተው ወሰዱ። ሰብር አደዲን ግን አስቀድሞ ስለሸሸ ሊያገኙት አልቻሉም።
በአፄ አምደጽዮን ላይ ጠላት ሁነው የተነሱት የቤተክህነቱ ባለስልጣናት በየገዳማቱና በየአድባራቱ ህዝቡ አንገዛም እንዲልና እንዲያምፅ ሰብከውት ስለነበር በሰሜን በፀለምት በጠገዴ በወገራ በደንቢያ የተሾሙ ሁሉ አመፁባቸው።
EthiopianKingAmdetsion
(Please download file to open)