አቶ ማሞ ውድነህ፡ ልክ በአደዋ ድል የመታሰቢያ ሣምንት፡ በየካቲት 23 ቀን 2004 ዓ.ም ከዚህች ዓለም ሲለዩን በጣም እያዘንን ነው። ከጥቂት ወራት በፊት ጋሽ ማሞን አግኝቼ ለማየት በመብቃቴ በጣም እድለኛ ነኝ። ነፍሳቸውን እግዚአብሔር ይማርልን!
የስድስት ልጆች አባት እና የአሥር የልጅልጆች አያት የሆኑት እኝህ ታላቅ ኢትዮጵያዊ ደራሲ፣ ተርጓሚ፣ ጋዜጠኛና የታሪክ ተመራማሪ፤ ትተውልን ከሄዱት የተለያዩ ጽሁፎቻቸው ለዛሬው ትውልድ ጠቃሚና ትምሕርታዊ የሆኑ መልዕክቶችን እናገኛለን።
ለምሳሌ፤“ዮሐንስ” በሚለው መጽሐፋቸው የሚከተለውን ማሳሰቢያ እናነባለን፡
በሥልጣኔ የተራመዱት የውጭ አገር መሪዎች በተለይ በያዝነው በሓያኛው ዘመን የሚገኙት ራሳቸው ታሪክ ሠሪ፥ የፖለቲክና የአስተዳደር ወይም የጦር አመራር ኃላፊ ሆነው አገራቸውን አገልግለው ወደ ዕድሜያቸው ፍጻሜ ላይ ሲቃረቡ ለመጭው ወይም ላሉበት ትውልድ መመሪያ ወይም መማሪያ የሚሆን ማስታወሻ በጽሑፍ አስፍረው በመጽሐፍ ቅጽ ያሳትማሉ።
የኛ መሪዎች፥ ታሪክ ሠሪነት ሳያንሳቸው በማናቸውም መስክ በሕይወታቸው የሠሩትን በጽሑፍ አስፍረው ለመጭው ትውልድ የማስተላለፉን ተግባር አልደረሱበትም።
ከሐያኛው መቶ ዓመት በፊት የነበሩት አባቶቻችን፥ አብዛኞቹ የሚያሳስባቸው ከምድራዊ ው ሕይወት የበለጠ የሰማያዊው ኑሮ ስለሆነ አብዛኛው ጽሑፋቸው የሚያተኩረው ከመንፈሳዊ ጽሑፍ ላይ በመሆኑ ያስተዳደሩን የፖለቲካውንና የጦርነቱን ታሪክ ያበረከቱት በመጠኑ ነው። እንደ አሁኑ ግንዛቢያችንና ፍላጐታችን የቄሥርን ለቄሣር… ስለሆነ ሁለቱም በየሙያውና በየመልኩ ቀደም ብሎ ባለው ዘመን በዝርዝር ቢጻፍ ኖሮ፥ ላሁኑ የዕውቀት አምሮታችን ሊያረካን በቻለ ነበር።
በአፄ ቴዎድሮስ የተተለመው ያገር አንድነትና የማዕከላዊ መንግሥት ግንባት የተጠናከረው ከዳግማዊ ምኒልክ በፊት ባፄ ዮሐንስ ዘመነ መንግሥት ነው። እኝህ አገር አፍቃሪ ንጉሠ ነገሥት፥ ባገር ወራሪዎች ላይ የሁለት ጊዜ ድል አድራጊነትን የተጐናጸፉ፥ በሙሉ ያስተዳደር ዘመናቸው ለኢትዮጵያ አንድነትን ጽናት ለሕዝብ ሕብረት የደከሙ፥ በመጨረሻም የሕዝባቸውን ጥቃት ለመመለስ ሲሉ በቁጭት ተነሣሥተው የራሳቸውን ሕይወት የሰዉ ናቸው።
“እንኳን ለመሬቷ ለጭብጥ አፈሩዋም ቢሆን ስሱ ነኝ” ብለው መተማ ድረስ ዘምተው ከሀገሪቷ ድንበር ላይ ስለወደቁት ዮሐንስ አራተኛ የሕይወትና የሥራ ታሪክ የቱን ያህል እናውቃለን? እስከዛሬ የቀረበልን ታሪካቸውስ በቂ ነው ወይ? በይበልጥ ልናተኩርበትስ አይገባም ወይ? እንደዚህ የመሳሰሉ ጥያቄዎች በብዙዎቹ ኢትዮጵያውያን አዕምሮ እንደሚመላለሱ ሁሉ በኔም ልቦና ካደሩ ዓመታት አልፈዋል። መልሶቹን ለማግኘትም ስል መጻሕፍት ማገልበጥ የእድሜ ጌቶች የሆኑ አዛውንቶችንና ምሑራንን መጠየቅ ከጀመርኩም እንደዚሁ አመታት አሳልፌያለሁ።
እንደ አለቃ ለምለም፥ እንደ አባ ኃይለማርያም፥ እንደ ቄስ ገበዝ ትክለ ሃይማኖት፥ እንደ አለቃ ዘዮሐንስ፥ እንደ አዝምች ገብረ ሚካኤል ግርሙ፥ እንደ ሊቀ መራዊ፥ እንደ መልአከ ብርሃኑ፥ እንደ ንቡረዕድ ኢያሱ፥ እንድ ልሳነ ወርቅ ገብረየሱስ፥ እንድ ዶክተር አባ ገርብረየሱስ ኃይሉ… የመሳሰሉት ታሪክ አፍቃሪዎች በግዕዝ፥ በአማርኛና ትግርኛ ቋንቋዎች የቻሉትን ያህል ስለአጼ ዮሐንስ ታሪክ ጽፈዋል። ግን የእነዚህ ሊቆች መዘክሮች ታትመው ለትውልድ አልተላለፉም። እንዲያውም አንዳንዶቹማ ባሕር ማዶ ተሻግረው የባዕዳን ንብረት ሆነዋል። ይህ ጉዳይ ባለፈው ስንጸጸት ለወደፊቱ እንዳይደገም የሚያስጠነቅቀን ይሆናል። ለሰነዶችና መዛግብት ከፍተኛ እንክብካቤ እንዲደረግ የደረስንበቱ ጊዜ በይበልጥ ያሳስባል።
በተለይ ከዐሥራ አምስተኛው ክፍለ ዘመን ጀምሮ በልዩ ልዩ ምክኒያቶችና ሁኔታዎች የተነሣ፥ በርካታ ታሪክ ተመራማሪዎችና አፍቃሪዎች ወደ ሀገሪቱ ገብተዋል። ብዙዎቹም መዘክሮቻቸውን አሳትመዋል። በዘመናችን ወደ ሀገራችን እየገቡ ያጠኑትን ታሪክ ካቀረቡት ሊቆች መካከል እንደ ሪቻርድ ፓንከርስት፥ ስቬን ሩቢንሰን፥ ዣንድ ዶሪስ ሐሮልድ ማርክስና ሐጋይ ኤሪሊክ ከዘመነ መሳፍንት ቀጥሎ የተነሡትን የቴዎድሮስን፤ የተክለጊዮርጊስን፥ የዮሐንስንና የምኒልክን ትሪክ ቀደም ካሉት ነገሥታት ለየት አድርገው በዝርዝር አቅርበውታል። ለዚህም ምክኒያታቸው ባዕዳን በሀገሪቱ ላይ ከመቼውም ጊዜ ይልቅ ሃይማኖትን ሽፋንና ምክኒያት በማድረግ የእጅ አዙርና ቀጥታ ወረራ የጀመሩበት፥ ቅኝ ገዥዎች አፍሪቃን ለመቀራመት ታጥቀው የተነሡበት፥ ሐሳበ–ብርቱዎችና ሐሳበ–ልሉዎች ከጠባብ ፈተና ጋር የተላተሙበት እጅግ አስቸጋሪ ወቅት ስለነበረ ነው። ይህ የታሪክ ምዕራፍ ደግሞ የሀገራችን የታሪክና የሥነ ጽሑፍ ባለሙያዎች በይበልጥ እንዲያተኩሩበት የሚያስገድድበትና የሚጋበዝበት አያሌ ምክንያቶችም አሉት።
ቋረኛው ካሣ፥ ላስቴው ጐበዜ፥ ተንቤኔው ካሣ፥ ተጉለቴው ምኒልክ ባንድ ወቅት ተወልደው ተከታትለውም ነግሠው፥ ተከታትለው አልፈዋል። እነዚህ ታላላቅ መሪዎች የሀገሪቱን አንድነትና ነጻነት ለማስከበር ከፍተኛ ተጋድሎ አድርገዋል።
እርግጥ ነው፥ አራቱም መሪዎች ቢሆኑ ከእነርሱ በፊት እንደነበሩት ነገሥታት የዘውድ ባለቤት ለመሆን እርስ በርሳቸው በሥውርና በግልጽ ተፎካክረዋል። ተዋግተዋል። ከእነርሱ በፊት የነበሩት ነገሥታት የሠሩትን ስሕተት እነርሱም አልፈጸሙትም ለማለት አያስደፍርም። ቴዎድሮስን ላስቴው ጐበዜና ተምቤኔው ካሣ ተባብረው ወግተዋቸዋል። እርሳቸው ከወደቁና ጐበዜ “ተክለጊዮርጊስ” ተብለው ከነገሡ በኋላም ተንቤኔው ካሣ ወግተው በትረ መንግሥታቸውን ቀምተዋል። ከዚያም ካሣ “ዮሐንስ” ተብለው ከነገሡ በኋላ ከተጉለቴው ምኒልክ ጋር ሲፎካከሩ፥ ሲታረቁ፥ ሲጋጩ፥ ሲካረሩ ሲዛዛቱ ዮሐንስ እስተወደቁ ድረስ ሆድና ጀርባ እየሆኑ ቆይተዋል።
ይህን ወድ ጐን ትተን ወይም በየትኛውም አገር የተፈጸመ የሰዎች ድክመት መሆኑን ተቀብለን፥ ሥራዎቻቸውን ስንመረምር ግን እኛንም ሆነ ተከታዩን ትውልድ የሚያኮራ የሀገሪቱን ታሪክ እጅግ የሚያደምቅ ፍሬ ነገር ትተውልን ማለፋቸውን ማስታወስ እንወዳለን። መሳፍንት የከፋፈሉዋትን ሀገር በአንድ ማዕከላዊ ጠንካራ መንግሥት እንድትመራ፥ ዳር ድንበሩዋ የተከበረና የታፈረ እንዲሆን ለማድረግ በመጀመሪያ የቋረኛው ካሣን ብርቱ ጥረት ጠይቋል።
ከአራቱ አጤዎች ሦስቱን የታላቅ ወንድም ያህል የሚበልጡት ቋረኛው ካሣ “ቴዎድሮስ” ተብለው ከነገሡበት ጊዜ ጀምሮ ሀገሪቱ አንድነቷ የጠነከረ፥ የግዛት ድንበሩዋ የታፈረ፥ ሕዝቡዋ በዕደ ጥበብ የበለጸገ፥ በነጻነቱና በእምነቱ ለበ–ሙሉ የሆነ እንዲሆንልቸው የከፈቱት ታላቅ ፈር የተወሰነ ውጤት ከማስገኘቱም በላይ፥ ደቆና ላልቶ የነበረውን የአንድነት ዓላማ ቀስቅሷል። ቀዝቅዞ የነበረውን የጀግንነት ወኔ አነሣሥቶ ዳኣኣዐር እሰከ ዳር አስተጋብቷል። የቴዎድሮስ ወራሾች ከነበሩት ሦስት ነገሥታትም መካከል የላስታው ጐበዜ “ተክለ ጊዮርጊስ” ተብለው ይንገሡ እንጂ ዘመነ–መንግሥታቸው አራት ዓመታት እንኳ ያልሞላ በመሆኑ ጐልቶ የሚታይ ውጤት ሳያሳዩ አልፈዋል።
ከእርሳቸው ቀጥለው በትረ–መንግሥቱን የጨበጡት የተምቤኑ ካሣ “ዮሐንስ” ተብለው ለዐሥራ ስምንት ዓመታት ኢትዮጵያን ሲመሩ፥ ቴዎድሮስ የተለሙትን ታላቅ ዕቅድ ተከትለው የሀገሪቱን ዳር ድንበት ወደጥንታዊ ክልሉ መልሰው፤ አንድነቱን አጽንተው በተለይም ደጋግሞ የመጣውን የሀገሪቱን ጠላት ደጋግመው ድል መተው የዛሬዋን ኢትዮጵያን ቀርጸው በመጨረሻም የሀገሪቱ ወሰን መሰበሩ፥ ጐንደር መደፈሩ አስቆጥቷቸው በመተማ ግንባር ጀግንነታቸውን በሕይወታቸው ዋጋ አስመስክረዋል።
ከእርሳቸው ቀጥለው ዙፋን የወረሱት ምኒልክም ቢሆኑ ያለፉትን ነገሥታት ዓላማ ተከትለው ታላላቅ ሥራዎች አሳይተዋል። የአራቱ መሪዎች ዓላማና እቅድ አንድ ቢሆንም ቅሉ ፍጻሜያቸው ደግሞ የተለያየ ነው። ቴዎድሮስ “እጄን ለማንም አላስጨብጥም” ብለው መቅደላ ላይ ራሳቸውን ሲገድሉ፥ ተክለ ጊዮርጊስ ደግሞ ከተንቤው ካሣ ጋር ጦርነት ገጥመው ከተማረኩ በኋላ ዐይኖቻቸውን ተከልለው በእስር ላይ ሆነው ከዚህ ዓለም በጣዕርና በስቃይ ሲለዩ፥ ምኒልክ ደግሞ ለብዙ ጊዜ በሕመም ተሰቃይተው በቤተ መንግሥታቸው ዐርፈው በክብር ተቀብረዋል። እስከዛሬ በየታሪካቸው መደምደሚያ ልይ የምናውቀውም ይህንኑ ነው። የዮሐንስ ፍጻሜ ግን፥ ከሦስቱም ለየት ያለና በሀገሪቱ ታሪክም ላይ ጐልቶ የሚታይበት ተጨማሪ ምክኒያት ያለው ነው።
በታሪክ ላይ የሚመሠረት ጽሑፍ ከፍተኛ ጥንቃቄ ይጠይቃል
የባለታሪኩን ቤት–ትውልድ አስተዳደጉን፥ አኗኗሩን ሥራውን የኖረበትንና የሠራበትን አካባቢ ማወቅን፥ ስለእርሱ የተጻፉትንና በሰሚ ሰሚ ከትውልድ ወደ ትውልድ በሰዎች አዕምሮ የተላለፉትን ትዝታዎች መሰብሰብን፥ እሱ በነበረበት ወቅት የነበረውን የሀገርና የዓለም ሁኔታዎች እንደዚሁም የቋንቋ ደረጃ፥ ሲሆን አጣርቶ ለማወቅ ያለዚያም የተቻለውን ያህል ለመቅሰም ጥረት ይጠይቃል።
ከዚህ ቀጥሎ ደግሞ፥ ሁኔታዎችን ሁሉ አገናዝቦ እውነተኛውን ድርጊት አዳብሮ፥ ሀገርን ባለ ታሪኩንና ትውልድን የሚያጎድፉ አሉ፥ ቧልቶችን ሽሮና ደምስሶ አኩሪ፤ አስተባባሪና አስተሳሳቢ በሆኑ ይትባህሎች ተክቶ ለማቅረ ደግሞ አርቆ አስተዋይነትና ጥንቃቄ የደራሲው ግዴታም ይሆናል። በተለይም ገና በማደግ ላይ ለሚገኙ አገሮች ይህ ግዳጅ በቀላሉ የማይታለፍ ይመስለኛል።
እኔም በትውልድ ሐረጋቸው ከታወቁ ጀግኖች ቤተሰብ፥ በልጅነታቸው የቤተክህነት ተማሪ፤ በሃይማኖታቸው ጽኑ የተዋህዶ ተከታይ፥ በአኗኗራቸው የሥነ ምግባር ተገዥ፥ በተግባራቸው መነኩሴ፥ በአመራራቸው አገር አፍቃሪና ዲፕሎማት፥ በሙያቸው የጦር መሪና ንጉሠ ነገሥት፥ የሆኑትን የአጼ ዮሐንስን እውነተኛ ታሪክ መነሻ በማድረግ፥ ከግል ግንዛቤ ጋር በማዛመድ፥ የአነበብኳቸውንና የሰማኋቸውን ትረካዎች አዋህጄ፥ የራሳቸውን የዮሐንስን ባሕርይ ለታሪካቸው ማንቀሳቀሻ በማድረግ፥ ጅማሬያቸውንና ፍጻሜያቸውን በዚህ ልቦለዳዊ ስልት አቅርቤዋለሁ።
አጼ ዮሐንስ በሃይማኖትና በሀገር ፍቅር ጽናታቸው እጅግ ብርቱ ነበሩ። በተለይም በሃይማኖት ላይ የነበራቸው ጽናት ለውድቀታቸው መፍጠንም ሆነ ለመሪነታቸው ኃይል ያሳደረባቸው ተጽዕኖ ከእርሳቸው በፊት በነበሩት ነገሥታት በእነ አጼ አምደጽዮን፣ በእነ አጼ በዕደማርያም፥ በእነ አጼ ንብለድንግል፥ በእነ አጼ ሚናስ፥ በእነ አጼ ገላውዴዎስ፥ በእነ አጼ ሱሱንዮስ ከደረሰው በአንዳንድ የአስመሳይ ካህናትና ባሕታውያን ተንኮል ሊያመልጡ አልቻሉም።
በትረካው ውስጥ እንደሚታየው፥ አጼ ዮሐንስን ለማሳሳትና ለመበቀል ባሕታዊ ተመስሎ ወደ ቤተ መንግሥታቸው የገባው ተንኮለኛ ካህን የዘረጋው ወጥመድ የያዘውና የጣለው አጼ ዮሐንስን ብቻ ሳይሆን አገርንና ወገንን ጭምር መሆኑን መረዳት ይኖርብናል።
በየግል እምነታችንና ፍላጐታችን የተመሠረተ ተንኮል፥ ቅናትና ምቀኝነት በሀገር፣ በነጻነትና በአንድነት ላይ የሚደርሰውን ጥፋትና ውድቀት በትክክል ለመገንዘብና ትላንት ወደተፈጸመው ስሕተት እንዳንወድቅ ለመጠንቀቅም ይህ ምሳሌ በይበልጥ ሊያሳስበን ይገባል።
የደራሲ ማሞ ውድነህ ገጸ በረከቶች
-
ሁለተኛው የዓለም ጦርነት
-
የሴቷን ፈተና
-
ከወንጀለኞቹ አንዱ
-
ቬኒቶ ሙሶሊኒ
-
የገባር ልጅ
-
ሁለቱ ጦርነቶች
-
አደገኛው ሰላይ
-
ዲግሪ ያሳበደው
-
ካርቱም ሔዶ ቀረ?
-
የ፮ቱ ቀን ጦርነት
-
የደቡብ ሱዳን ብጥብጥ
-
ብዕር እንደዋዛ
-
ሞንትጐመሪ
-
የኤርትራ ታሪክ
-
“የኛው ሰው በደማስቆ“
-
የ፪ ዓለም ሰላይ
-
ምጽአት–እሥራኤል
-
ሰላዩ ሬሳ
-
የ፲፯ቱ ቀን ጦርነት
-
የካይሮ ጆሮ ጠቢ
-
የበረሃው ተኰላ
-
ዘጠና ደቂቃ በኢንተቤ
-
ጊለን–የክፍለ ዘመኑ ሰላይ
-
የኦዲሣ ማኅደር
-
ከታተኞቹ
-
ከሕይወት በኋላ ሕይወት
-
ስለላና ሰላዮች
-
ምርጥ ምርጥ ሰላዮች
-
ዕቁብተኞቹ
-
አሉላ አባነጋ
-
የሰላዩ ካሜራ
-
“ሰላይ ነኝ“
-
በዘመናችን ከታወቁ ሰዎች
-
ዕድርተኞቹ
-
ሾተላዩ ሰላይ
-
ማኅበርተኞቹ
-
በረመዳን ውዜማ
-
የበረሃው ማዕበል
-
ኬ.ጂ.ቢ.
-
ሲ.አይ.ኤና ጥልፍልፍ ሲሆኑ
-
ዩፎስ–በሪራ ዲስኮች
-
መጭው ጊዜ
-
እና ይኸው ራሱ
-
ዮሐንስ ናቸው ፤
-
የአሮጊት አውታታ
-
እኔና እኔ
-
ኤርትራና ኤርትራውያን
-
ሞት የመጨረሻ ነውን?
_________________________________________