Addis Ethiopia Weblog

Ethiopia's World / የኢትዮጵያ ዓለም

  • June 2023
    M T W T F S S
     1234
    567891011
    12131415161718
    19202122232425
    2627282930  
  • Archives

  • Categories

  • Recent Posts

Posts Tagged ‘Enochian Calendar’

ትክክለኛው የዘመን አቆጣጠር

Posted by addisethiopia / አዲስ ኢትዮጵያ on December 31, 2010

  • ኢትዮጵያ እና ኢትዮጵያዊነት ከሚለው የንቡረ እድ ኤርምያስ ከበደ ወልደ ኢየሱስ መጽሐፍ የተወሰደ

በአረማዊነት ባህል፡ በክዋክብት ሥነ እውቀት ላይ የተመሠረተው የምዕራባውያን የዘመን አቆጣጠር፡ ከኢትዮጵያውያኑ የዘመን አቆጣጠር፡ የሚለይበት ባሕርይና አኹን ያለበት ቀውስ የደረሰበት ለምን ይሆን?

ኢትዮጵያውያን፡ በቅዱሱ ኪዳን ሃይማኖታቸው ላይ የመሠረቱትን፡ ይህን የጊዜ አቆጣጠር ሥርዓት፡ ምዕራባውያን፡ ኦርቶዶክሳውያን የተባሉት አብያተ ክርስቲያናት ጭምር፡ በአረማዊው፡ ዮልየስ ቄሣርና ጎርጎርዮስ (ግሬጎሪ) ፩፫ኛ በተባለው፡ በካቶሊካዊው ጳጳስ ስሞች እየሠየሙ፥ በየጊዜው እየለዋወጡና በመጨረሻ፡ ፰ ዓመታት ከ፲ ቀናት ያህል አክለውበት መቆየታቸው ይታወቃል። በዚህ የአቆጣጠራቸው ስልት፡ የጌታችን የኢያሱስ ክርስቶስን የልደት ቀን፡ ከ፬ እስከ፯ ዓመታት ለሚደርስ ዘመን፡ ከፍ አድርገው እንዲጨምሩ በመገደዳቸው፡ ይህን፡ ሰው ሠራሽ ቀውስ አስተካክለው ለማስታረቅ አቅቷቸው፡ እነሆ፡ እስካሁን ሲባዝኑ ይገኛሉ። በዚህ፡ በእነርሱው አቆጣጠር፥ ጌታ፡ የተወለደው፡ በ፬፥ በ፮ ዓመተ ምሕረት ላይ ሳይኾን አይቀርምከማለት በስተቀር፡ እርግጠኛውን ቀን፡ በቁርጥ ሊወስኑ ሳይቻላቸው ቀርቷል።

ይህ ቀውስ የተፈጠረባቸው፡ የጌታን የልደት ዓመት፡ አንድ ብለው መቁጠር ከጀመሩ በኋላ፡ ያ፡ የዓመተ ምሕረት መነሻ ዘመን፡ በአረማዊነት ዘመናቸው፡ ጁልያንበሚል ስምና በተለያየ ስልት ይጠቀሙበት በነበረው የአቆጣጠር ሥርዓታቸው፡ በ፬፥ በ፯ ዓመታት ላይ ውሎ ስላገኙት ነው።

ሌላው፡ ይህን ችግር የፈጠረባቸው ምክንያት፡ የምዕራባውያን የጊዜ አቈጣጠር፡ እንደ ኢትዮጵያውያኑ፡ በአንድ መሠረት ላይ ታንጾና በአንድ በተስተካከለ ሥርዓት ተቀምሮ የሚመራ ባለመኾኑ ነው። ይህንም፡ ከዚህ የሚከተለውን ማነጻጸሪያ ሓተታ በመመልከት መረዳት ይቻላል።

ኢትዮጵያውያን፡ የእግዚአብሔር ገነትተተከለባት፡ አዳምና ሔዋን የተፈጠሩባት አገራቸው የምትገኘው፡ በምድር ማዕከል ወይም መቀነት ክልል ውስጥ ስለኾነ፡ የጊዜ አቈጣጠራቸው ሥርዓት፡ መዓልቷና ሌሊቷ፡ ዓመቱን ሙሉ፡ በ፲፪፡ በ፲፪ ሰዓታት፡ እኩል በተከፈለበት የአሠፋፈር ስልት ላይ ተመሥርቶ፡ የባሕረ ሓሳቡ ቅመራ፡ ሥርዓቱን ጠብቆ፡ ያለችግር ይካኼዳል። ይኽውም፡ ወደኋላ፡ ወደረቂቃኑ ሳንኼድ፡ ከሣልሲት ተነሥተን፡ እስከ ዓመት ብንቈጥር እንኳ፡ ቀመሩ፡ የተስተካከለ ኾኖ እናገኘዋለን። ማለትም፡ ፷ (ስድሳ) ሣልሲታት፡ ፩ (አንድ) ካልዕት (second)፥ ፷ ካልዕታት፡ ፩ ደቂቃ፥ ፷ ደቂቃት፡ ፩ ሰዓት፡ ፳፬ ሰዓታት፡ ወይም ፷ ኬክሮስ፡ ፩ ዕለት፡ ፩፪ ሰዓታትን የያዘው፡ የብርሃን ጊዜ፡ መዓልት፥ ጨረቃ እንድትሠለጥንበት የተፈጠረችበት፡ ፩፪ ሰዓታትን የያዘው፡ የጨለማ ጊዜ፡ ሌሊትይባላል።

የመዓልቱ የጊዜ አቆጣጠር፡ የተፈጥሮውን ሥርዓት በመከተል፡ ከቀትር በፊትእና ከቀትር በኋላተብሎ፡ ፀሓይ፡ ጮራዋን በምትፈነጥቅበት፡ በንጋቱ ፩ ሰዓት ይጀምርና፡ በምትጠልቅበት፡ በምሽቱ ፲፪ ሰዓት ያበቃል፡ የሌሊቱም ጊዜ፡ እንደዚሁ፡ እስከእኩለ ሌሊት ድረስ፡ ከማታው፥ ከእኩለ ሌሊት በኋላ ደግሞ፡ ከሌሊቱእየተባለ፡ ጨረቃ ከምትታይበት፡ ወይም ጨለማው ከሚጀምርበት፡ ከምሽቱ፡ ፩ ሰዓት ይነሣና፡ ጎህ በሚቀድድበት፡ በንጋቱ ፲፪ ሰዓት ይቆማል።

በዚህ መሠረት የተደለደለችው፡ አንዲቱ ዕለት፡ ሰባት ስትኾን፡ ፯ቱ ዕለታት፡ ፩ ሳምንት ይኾናሉ።

የምዕራብውያኑ ግን፡ እንዲህ አይደለም። ምዕራባውያን፡ የሰሜኑንና የደቡብን የመሬት ዋልታ ተከትለው፡ በሰሜንና በደቡብ ክፍላተ ዓለማት፡ የሚኖሩ በመኾናቸው፡ ኢትዮጵያውያን፡ ክረምት፥ መፀው፥ በጋ፥ ጸደይ እንደሚሉት፡ የእነርሱም ዓመት፡ Winter(ዊንተር) Spring (ስፕሪንግ) Summer (ሰመር) Autumn (ኦተምን) በተባሉ፡ በአራት የተለያዩ ወራት ተከፋፍሎ፡ በክረምቱ፡ ሌሊታቸው፡ እስከ ፭ ሰዓታት የሚጨምርበት፥ እንዲያውም፡ ወደሰሜኑም ኾነ ወደ ደቡቡ የመሬት ዋልታ ጫፍ እይተጠጉ በኼዱ መጠን፡ የሚቀነሱት፡ ወይም የሚጨመሩት ሰዓታት እያደጉ ይኼዱና፡ ወደ መጨረሻው ጽንፍ ላይ ሲደርስ፡ ከናካቴው፡ ፮ ወራት ሙሉ፡ ሌሊት ብቻ፥ ወይም መዓልት ብቻ ይኾናል።

ይህም ማለት፡ ይህ ኹኔታ፡ በሰሜኑና በደቡቡ ክፍላተ ዓለም፡ በዓመቱ ውስጥ፡ እንዲህ ስለሚፈራረቅ፡ የክረምቱ ብርዳማ ጠባይ፡ ቀደም ብሎ እንደተገለጸው፡ የሰሜኑን ክፍል በሚያጠቃበት ጊዜ፡ በደቡቡ ክፍል ደግሞ፡ የበጋው ፀሓያማ ጠባይ ይሰፍናል ማለት ነው።

ይህ ብቻ ሳይኾን፡ በዓመት፡ ሁለት ጊዜያት፡ በየ፮ ወሩ፡ የሰዓት አቆጣጠራቸውን፡ እንደየክፍለ ዓለማቸው አቀማመጥ፡ በ፩ ሰዓት ያሳድጉታል፡ ወይም በ፩ ሰዓት ይቀንሱታል።

በኢትዮጵያውያን ዘንድ፡ ፯ቱ የሳምንቱ ቀኖች፡ የእግዚአብሔር፡ የሥነ ፍጥረት ሥራው፡ በተራና በቅደም ተከተል የተካሄደባቸውንና በቅዱሳት መጻሕፍት የተመዘገቡትን የዕለታት ስም እንደያዙ፡ የአዳምና ሔዋን ቋንቋ በሆነው፡ በግእዝ፡ አሐዱአንድ፡ ወይም፡ መጀመሪያ ቀንለማለት፡ እሑድ፥ ቀጥሎ፡ ሁለት፥ ወይም፡ ሁለተኛ ቀንለማለት፡ ማግሰኞ፡ ቀጥሎ፡ አራት፥ ወይም፡ የሰንበት መግቢያ፥ ወይም፡ የሳምንቱ ጊዜ፡ የሚጠልቅበት ቀንለማለት፡ ስድስተኛው ቀንዓርብ፥ በሰንበት ጌታ፡ በኢያሱስ ክርስቶስ ትንሣኤ፡ ወደዘለዓለማዊነትከመለወጧ በፊት፡ ቀድሞ የነበረችበትን ሁኔታ ለማስታወስ፡ ሰባተኛዪቱን የሰንበት ቀንቅዳሜብለው ይጠርዋቸዋል።

ምዕራባውያን ግን፡ ለእነዚሁ የሳምንት ቀኖች፡ የሰጧቸውን የአረማውያን ጣዖታት አማልክቶቻቸውን ስም እንመልከት!

  • Sunday: Sun’s day (ሳንዴይ) ማለት የፀሓይ ቀን

  • Monday: Moon’s day (ማንዴይ) የጨረቃ ቀን፥

  • Tuesday: Tui’s day (ቱዩስዴይ)፡ ማለት፡ የጦርነቱ አምላክ፡ የቲዩ ቀን፥

  • Wednesday: Woden’s day (ዌድንስዴይ)፡ ማለት፡ የታላቁ አምላክ የውድን ቀን፥

  • Thursday: Thor’s day (ተርስዴይ)፡ ማለት፡ የነጎድጓዱ አምላክ፡ የቶር ቀን፥

  • Friday: Frigg’s day (ፍራይዴይ)፡ ማለት የታላቁ አምላክ፡ የዎድን ሚስት፡ የፍሪግስ ቀን፥

  • Saturday: Saturn’s day (ሳተርዴይ)፡ ማለት፡ የሰማዩ ኮከብ፡ የሳተርን ቀን።

በኢትዮጵያውያን ዘንድ፡ ፴ ዕለታት፡ ፩ ወር ሲኾኑ፥ ፲፪ ወራት እና ፭ ዕለታት ተሩብ ደግሞ፡ ፩ ዓመት ይኾናሉ። ፭ቱ ዕለታት ተሩብ፡ ጳጉሜይባላሉ። ጳጉሜ፡ የቃል ለቃል ትርጉሙ፡ ተውሳክጭማሪተረፍትርፍማለት ነው። ፲፪ቱ የምዕራባውያን ወሮች ግን፡ ፳፰፡ ዕለታትን፥ በየአራት ዓመቱም፡ ፳፱ ዕለታትን ከያዘውና (February – ፌብሩአሪ) ከሚባለው፡ ከአንደኛው ወር በቀር፡ እኩሌቶቹ፡ በ፴፥ የቀሩትም፡ በ፴፩ ዕለታት ተመድበው፡ ይህን በመሰለ የተዘበራረቀ መልክ ይቆጠራሉ።

በኢትዮጵያውያን በኩል፡ ከመስከረም እስከ ነሓሴ ድረስ ያሉት፡ ፲፪ቱ ወሮቻቸውና ጳጉሜ፡ እያንዳንዳቸው የሚጠሩበት ስም፡ ከእግዚአብሔር ከተሰጣቸው፡ የተፈጥሮ ጸጋቸው ጋር የተያያዘው ገጽታቸውን የሚያሳይ ትርጉም ያለው ሲኾን፡ በኢትዮጵያውያን የወራት አመዳደብ መሠረት፡ ከ September (ሴፕቴምበር) መስከረም እስከ እስከ August (ኦገሥት) ነሓሴ ድረስ ያሉት የምዕራባውያኑ ወሮቻቸው ግን እንደሳምንቱ ቀኖቻቸው ኹሉ፡ የተሠየሙት፡ በጣዖቶቻቸውና እንደአማልክት ይሰግዱላቸው በነበሩት ገዢዎቻቸው ስም ኾኖ ይገኛል።

ይኽውም፡ መስከረምን ከኢትዮጵያውያን፡ August(ኦገሥትን) ነሓሴን ደግሞ ከምዕራባውያን፡ ለምሳሌ ያህል ወስደን ብንመለከታቸው መስከረም፡ በኢትዮጵያኛ፡ ከረመወይም፡ ክረምትን አሳለፈከሚለው ግሥ ወጥቶ፡ ክረምቱ የሚያበቃበት፡ ማለትም፡ የዝናሙ ጠል አብቅቶ፡ የፀሓይ ብርሃን የሚፈነጥቅበት፡ የዓባይና የሌሎቹ ወንዞች ሙላት መጉደል የሚጀምርበትና ፍጥረቱ ኹሉ፡ ከተሸሸገበት በዓቱ እየወጣ፡ እርስ በርሱ የሚገናኝበት፡ አዲሱ ዓመት፡ የሚገባበት ማለት ነው። መስከረም ጠባየሚባለውም ለዚህ ነው። በምዕራባውያን ዘንድ ግን፡ August (ኦገሥት)፡ ስለወሩ ኹኔታ፡ ምንም ትርጉም የሌለው ኾኖ፡ እንደጣዖት ይመለክ ለነበረው፡ ለአረማዊው ርእሰ ነገሥት (Emperor): ለአውግሥጦስ ቄሣር፡ በመታሰቢያነት የተሰጠ ወር መኾኑን ብቻ ያስረዳል።

የኢትዮጵያውያን ዓመት የሚጀምረው፡ በመስከረም፡ የሚያበቃውም፡ በጳጉሜሲኾን፡ የምዕራባውያ ኑ ግን፡ በእነርሱ January (ጃንዋሪ)፡ ማለትም፡ በጥርይጀምርና፡ በDecember (ዲሴምበር)፡ ማለትም በታኀሣሥይጨርሳል። ስሙን በመታሰቢያነት፡ January (ጃንዋሪ) ብለው፡ ለዓመቱ የመጀመሪያ ወር የሰጡለት፡ Janus(ጃኑስ)፡ ለሮማውያን፡ ታላቁ ጣዖታቸው እንደነበረ፡ ቀደም ብሎ ተመልክቷል።

በኢትዮጵያውያን ዘንድ፡ ፬ ዓመታት፡ ፩ ዐውደ ዘመን ይኾናሉ። ይህም፡ እያንዳንዱ ዓመት፡ ፫፻፷፭ ከሩብ ዕለታት፡ ወይም ከ፮ ሰዓታት፡ ወይም ከ፲፭ ኬክሮስ ያለው ሆኖ፡ ዘመነ ማቴዎስዘመነ ማርቆስዘመነ ሉቃስእና ዘመነ ዮሓንስተብሎ ተሠይሟል፡ እነዚህ፡ የ፬ቱ ዓመታት ጳጉሜዎች ሰዓታት ሲደመሩ፡ ፩ ዕለት የሞሉና፡ በ፬ኛው ዓመት፡ በዘመነ ዮሓንስ መግቢያ፡ ፮ ዕለታት በመሆን፡ የባሕረ ሃሳቡ ቅመራ ይካተታል፡ የዘመን አቆጣጠሩም ዐውድ፡ እንዲህ በየአራት ዓመታቱ ይዘጋል።

ስለዚህ፡ የግሬጎሪወይም ግሬጎሪያንተብሎ የሚጠራው፡ የምዕራባውያን፡ የጊዜ አቆጣጠር ባህል፡ እንዲህ፡ ምስቅልቅሉ የወጣ በመሆኑ፡ በእርሱ ሰበብና ጠንቅ፡ ጽኑ የሆነው ሃይማኖታዊና ተፈጥሮአዊ መሠረት ያለው፡ የኢትዮጵያ የዘመን አቆጣጠር ሥርዓት፡ ሊቃወስ ቀርቶ፡ ሊነካ እንኳ፡ ከቶ አይገባም።


Posted in Ethiopia | Tagged: , , , , , | Leave a Comment »

 
%d bloggers like this: