ከአራት ዓመታት በፊት፡ በጾመ ነነዌ ዕለት የኢትዮጵያ አየር መንገድ በእርኩስ ኃይሎች ቤይሩት ከተማ ተቃጠለ፣ ከዚህ ድርጊት በኋላ በየዓመቱ በነነዌ የፆም ሰሞን ከአየር ጋር / ከአውሮፕላን ጋር የተያያዙ አደጋዎች በየቦታው ተከስተዋል። ለምሳሌ፦
በ2011ቱ ነነዌ
አውሮፕላኖች ተከስክሰው ተሳፋሪዎች ሕይወታቸውን አጥተዋል
በ2012ቱ ነነዌ
በ2013ቱ ነነዌ
አሁን በጾመ ነነዌ ሳምንት (መስቀል ኢየሱስ) በአየር መንገዳችን ላይ በጣም ግራ የሚያጋባ ድርጊት ተፈጸመ።
ረዳት ፓይለቱ ጠላፊ መሆኑን ስሰማ ወዲያው የመጣልኝ፡ “ምናልባት የሕሊና በሽታ ደርሶበት ይሆናል! እንዲያውም የ “Manchurian Candidate” ሊሆን ይችላል” የሚለው ሃሳብ ነበር።
ይህ የጠለፋ ተግባር በሱዳን ዓየር፡ በዓባይ ወንዝ ከፍታ ላይ እንደተካሄደ ተገልጿል። ታዲያ በዚህ ወቅት በረዳት ፓይለቱ ላይ ምን አይነት ድርጊት ተፈጽሞበት ይሆን? “Hypnotize” ተደርጎ ይሆን? “Manipulate” ተደርጎ ይሆን? ጣልያናዊው ፓይለትስ ምን ዓይነት ሚና ተጫውቶ ይሆን?
ግለሰቡ ‘ጤናማ‘ እንደሆነ፡ ነገር ግን በአጎቱ ሞት ተጨንቆ / ተረብሾ እንደነበር ተገልጧል። ምንም እንኳን አስቀድሞ መፍረድ ተገቢ ባይሆንም፣ ግለሰቡ የፈጸመው ተግባር ግን የወንጀለኛነት፣ የከዳተኝነት ባሕርይ የያዘ ነው። በአገሩ ላይ ይህን መሰሉን ጥራዝ–ነጠቅ የከዳተኝነት ተግባር የሚፈጽም፣ አብዛኛው የአገራችን ሕዝብ ያላገኘውን ዕድልና ገፀበረከት አግኝቶ አሳፋሪ በሆነ መልክ በፈቃዱ ወደገደል የሚጥል ምስጋና–ቢስ ግለሰብ ነው። ከጀግኖቹ የምድር ባቡሮቻችን / ሯጮጫችን ጎን በአፍሪቃ አየር ለመላው አፍሪቃውያን መኩሪያ የሆነውን አየርመንገዳችንን ባላጋጩ አለም ዘንድ እንድንዋረድበት ማድረጉ እጅግ በጣም፡ በጣም የሚያሳዝን ነው። በተለይ፡ አሁን እንደ ግብጽ የመሳሰሉት ጠላቶቻችን የተንኮል መርዛቸውን ባገራችን ላይ ከያቅጣጫው በመርጨት ላይ በሚገኙበት ወቅት ይህን መሰሉን ተግባር መፈጸሙ ምሕረት የሚያስከለክለው ይሆናል። ይህ ጠለፋ፣ በሕዳሴው ግድብ ላይ ጥቃት ለማድረስ ከሚሻ የግብጽ ቅጥረኛ ጋር ተነጻጻሪ ነው።
በተለያዩ አጋጣሚዎች ከብዙ አገር ሰዎች ጋር አብሬ ለመማር፣ ለመሥራትና ለመኖር፡ አገሮቻቸውንም ለመጎብኘት እድሉ ነበረኝ፤ ታዲያ ከዚህ ሁሉ ለመማር የበቃሁት፤ እንደ አገር ሰው ማንም እንደማይሆነን፣ እንደ አገራችን የትም ሌላ አገር ተድላ፣ ደስታና የመንፈስ ተሃድሶ ልናገኝ እንደማንችል ነው። ሆኖም፤ በአገራችን እንደምንደሰት ሁሉ እንደ አገራችን በይበልጥ የምንከፋበት ሌላ ቦታ የለም። በተለይ መጨረሻ ጊዜ በአንዳንድ ወገኖቻችንን ዘንድ ትህትና፣ መተማመን እና መከባበር እየጠፋ፣ ፍቅር እየቀዘቀዘች መምጣታቸው በጥልቁ ያሳስበኛል።
ባለፈው ዓመት፣ ከአንድ አነስተኛ የፍራፍሬ መደበር ፊት ለፊት በሚገኘው የጫማ መጥረጊያ ቦታ ቁጭ ብዬ በመደብሩ የሚካሄደውን መስተንግዶ እከታተል ነበር። አንድ ወገናችን ቆሞ እንዲያስተናግዱት ወደ 10 ደቂቃ ያህል ቆሟል፣ ከእርሱ በኋላ ሁለት አረቦች/ቱርኮች እንደመጡ የእስላም ቆብ የደፋው የመደብሩ ባለቤት ቶሎ ቀርቧቸው ሲያስተናግዳቸው አየሁ። አላስቻለኝም፣ ከጫማ መጥረጊያው ተነስቼ ፍራፍሬው የተቀመጠበትን መደርደሪያ ወርውሬ በመጣል፣ በባለቤቱ ላይ ያልተለምዶዬ ጩኽቴን ጀመርኩ፤ “ለምንድን ነው ወገናችሁን የማታስቀድሙት?” “ቱርኩም አረቡም የራሱን ወገን እንጂ ሌላውን በፍጹም አስቀድሞ አያስተናግድም እኮ፡ ምናለ ወገናችሁን ብታከብሩ?!” አልኩ። የባለመደብሩ ሚስት መሰለችኝ እየተጸጸተሽ፡ “አዎ! አዎ!” አለች። ይህን መሰሉ ኩፉኝ በየሱቁ፣ በየምግብ እና ቡና ቤቱ፣ በየሆቴሉ ሁሉ በጣም እንደተስፋፋ ከብዙ ሰዎች ሰምቻለሁ። ይህ በጣም አሳሳቢና አሳዛኝ ጉዳይ ነው።
የረዳት ፓይለቱም ተግባር በጣም የሚያሳስብ ነው። ከጠለፋው ሌላ የሚያስገርመው ነገር፡ ክሣምንት በፊት በስደተኞች ላይ ጥብቅ ሕግ ለማውጣት ሬፈረንደም ወዳካሄደችበት ወደ ስዊትዘርላንድ ሄዶ የፖለቲካ ጥገኝነት ለማግኘት መሻቱ ነው።
ይህ ጠለፋ የሚያሳያን ሌላው ነገር፣ ከዚህ በፊት በተደጋጋሚ እንደምንሰማው “ድኽነት” ለኢትዮጵያውያን መሰደድ ዋናው ምክኒያት አለመሆኑን እና ከፊሉ ሕዝባችን ለከፍተኛ የመንፈሣዊ ቀውስ መጋለጡን ነው።
ሌላ የሚያሳዝነው፡ ጠላፊው ይህን ቅሌታማ ተግባር ከፈጸመ ከጥቂት ሰዓታት በኋላ፣ የጠላፊው ማንነት ከመታወቁ በፊት፣ ቀደም ሲል ከዋሃቢ ጠላቶቻችን ጎን ሰልፍ ሲወጡ የነበሩት የ ‘ሰማያዊ‘ ፓርቲ መሪ የኢትዮጵያውያንን ውድቀት ከሚሹት የውጭ መገናኛ ብዙኃን ወኪሎች ጋር የአንድ ንጹህ–ኢትዮጵያዊ ስነምግባር መንጸባረቂያ ያልሆነ መግለጫ መስጠታቸው ነው። በእውነት ይህ ተግባራቸው “ግብዝ! ቅሌታም!” ያሰኛቸዋል።
ስዊዘርላንዶችን በጣም እያጠያየቀ ያለው ነገር በስዊትዘርላንድ የአየር ክልል የኢትዮጵያ አየር መንገድን ያጀቡት የጦር አውሮፕላኖች የስዊትዘርላንድ ሳይሆኑ የጣልያንና የፈረንሳይ መሆናቸው ነው። ለካስ የስዊትዘርላንድ ተዋጊ አውሮፕላን ፓይለቶች ገና እንቅልፍ ላይ ነበሩ፤ ከጠዋቱ 2 ሰዓት በፊት ሥራቸውን አይጀምሩም ነበርና።
በሌላ በኩል ግን፡ ይህን የጠለፋ ክስተት በሚመለከት አንድ የምጠይቀው ጥያቄ አለ፦
- ‘ድኻዋ‘ አገራችን ያሰለጠነቻቸው የአየርመንገዳችን ፓይለቶችና ቴክኒሻኖች ለተሻለ “የምሥር ወጥ” ሲሉ አገራቸውን በመክዳት ወደ ‘ሃብታም‘ የአረብ አገራት በብዛት ይጎርፋሉ፣ በተቃራኒው ደግሞ አውሮፓውያን ፓይለቶች የኢትዮጵያን አውሮፕላኖች እንዲያበሩ ይደረጋሉ። ይህ እንዴት ሊሆን ቻለ? ይህ ጠለፋ በዕጥፍ እንድንዋረድበት ካደረጉን ተግባሮች መካከል፣ ፓይለቱ ጣልያናዊ መሆኑን መላው ዓለም መስማቱ ነው። ‘ኢትዮጵያ አውሮፕላን አላት እንዴ?’ ‘አህ፡ ኢትዮጵያውያን ማብረር ስለማይችሉ ፈረንጅ ቀጥረዋል!” የሚሉትን የጭፍኖች ትችት በየቦታው በማንበብ ላይ ነን። ከ50 ዓመታት በፊት እነ ኔልሰን ማንዴላ የኮሩበት ዓየር መንገዳችን አሁን እንዴት ፈረንጆችን ለመቅጠር በቃ?
“በዚያን ጊዜም ብዙዎች ይሰናከላሉ እርስ በርሳቸውም አሳልፈው ይሰጣጣሉ እርስ በርሳቸውም ይጣላሉ፤ ብዙ ሐሰተኞች ነቢያትም ይነሣሉ ብዙዎችንም ያስታሉ፤ ከዓመፃም ብዛት የተነሣ የብዙ ሰዎች ፍቅር ትቀዘቅዛለች። እስከ መጨረሻ የሚጸና ግን እርሱ ይድናል።” [ማቴዎስ ፳፬᎓፲፥፲፫]
Tears of Eritrea — የሀበሻ እምባ
__
Like this:
Like Loading...