VIDEO
በአሜሪካኑ ቴሌቪዥን፡ በ “ ታሪክ ጣቢያ ” (History Channel) “The Bible ” “ መጽሐፍ ቅዱስ ” የተሰኘ አንድ ባለ አሥር ሰዓት ፊልም እስከ መጪው የፈረንጆች ፋሲካ ድረስ እሁድ እሁድ በመታየት ላይ ነው። ይህ ፊልም፡ እንደ ‘ አሜሪካን አይድል ” የመሳሰሉትን ተወዳጅ የቴሌቪዥን ፕሮግራሞች በተመልካች ብዛት የቀጣ ከመሆኑም ሌላ፡ የመጸሐፍ ቅዱስን ባለ ታሪኮች ማን እንደተጫወተ / መጫወት እንደነበረበት በመርመር የሜዲያውን ዓለም ስሜታዊ በሆነ መልክ በማወያየት ላይ ይገኛል።
የብሉይ እና አዲስ ኪዳናትን ታሪኮችና መልዕክቶች ለማስተፋፈል ታስቦ የተሰረውን ይህን ፊልም መቅረጽ የጀመሩት ገና ፕሬዚደንት ኦባማ ለፕሬዚደንት ከመብቃታቸው በፊት ቢሆንም፡ ፊልሙ ላይ የ ሰይጣን ባለ ታሪክነቱን የሚጫወተው ከመካከለኛው ምስራቅ የመጣ ተዋናይ ከኦባማ ጋር ይመሳሰላል በማለት ብዙዎቹን እያነጋገረ ነው።
ነጭ ክርስቶስ፡ ጥቁር ሰይጣን
“አፍሪካዊ – አሜሪካኖች ፊልሙ ላይ ያሉትን መጥፎ መጥፎዎቹ ሰዎች ሲመለከቱ፡ ሁሉም እነርሱን የሚመሳሰሉ ገጽታ አሏቸው። ታዲያ አንዲት ህጻን ልጅ፡ “ ለምንድን ነው ሁልጊዜ ጥሩዎቹና ክርስቶስ ፈረንጆች የሚሆኑት ? ሰይጣን ደግሞ ኦባማን የሚመስለው ?” በማለት ታላቋን ጠየቀች። እሷም፡ “ ፈረንጆች ሁልጊዜ ፈረንጅ የሆነ ነገር ነው የሚሠሩት !” ብላ መለሰችላት። ” ይላል ክርስቲያን ሳይንስ ሞኒተር ።
እየሱስ ክርስቶስ ማን እንደነበር ከኢትዮጵያውያን የበለጠ የሚያውቅ ይኖራልን ?
በሚከተለው የ ንቡረ እድ ኤርሚያስ ከበደ ጠቃሚ ትምሕርት ሙሉ በሙሉ እስማማለሁ፦
“ ለአብርሃም፥ ለይስሓቅና ያዕቆብ በገባላቸው ቃል ኪዳን ምክንያት፥ እንዲሁም ስለስሙ ሲል እግዚአብሔር ለእሥራኤል ሕዝብ በነፍስና በሥጋ፥ በመንፈስም የሰጣቸው የቃል ኪዳን ጸጋና በረከት ዘርና መንግሥት፡ ኹሉም ወደ ኢትዮጵያና ወደ ኢትዮጵያውያን ተመልሰው ለእነርሱ የኾነበት የመለኮት ዕፁብ ድንቅ ሥራ የተገለጠበት፥ ኢትዮጵያንና ኢትዮጵያዊነትን በሚመለከት ቀደም ብሎ በአብርሃም ( በኢትዮጵያውያኖቹ በ መልከ ጼዴቅ፥ በ አቤሚለክ እና በሁለተኛ ሚስቱ በኬቱራ በኩል ) ቀጥሎም በሙሴ ( የሙሴ ባለቤት ሲጶራ ኢትዮጲያዊት ነበረች፣ ሙሴም ለ 40 ዓመታት ያህል ኢትዮጵያን በንጉሥነት አገልግሏል፡ የአብርሃምና ኬቱራ ዘር ኢትዮጵያዊው ዮቶር መምህሩ ነበር ) ሰውነትና ሕይወት ላይ ደርሰው የታዩትንና እነርሱን የመሰሉትን፥ ያለፉትን ኹሉ በበለጠ አጠናክሮ የሚያጸና ሌላ አራተኛ ትንግርት ደግሞ አለ።
ያም የመለኮት ዕፁብ ድንቅ ሥራ የተገለጠው በታላላቁ ሊቃውንት፥ በታወቁት ከበርቴዎችና በገናናዎቹ ኃያላን ዘንድና ላይ አይደለም፥ በቤተ ብዕል በቤተ ክህነት እና / ወይም በቤተ መንግሥት አዳራሾችም ውስጥ አይደለም። ከብቶቹን በሜዳ አሰማርቶ ለሚጠብቅ ለአንድ ተራ ብላቴና እረኛ ነበር እንጂ። የዚያ እረኛም ስም፡ “ ዳዊት ” ነበር።
ይህ ጻድቅና ነቢይ፡ ከኢትዮጵያዊውና “ አቤሚሌክ ” የሚል ስም ካለው የትውልድ ሓረግ የተወለደ በመኾኑ ኢትዮጵያዊነቱ በዘሩ ብቻ ሳይኾን እውነተኛ ሃይማኖቱና ምግባሩ በታላላቅ የገድል ፈተናዎቹ ስለተረጋገጠለት እግዚአብሔር ለሉዓላዊው አገልግሎትና ክብር መርጦ ሾመው። አዎን ! ከበግ እረኝነት ጠርቶ በእሥራኤልና በይሁዳ ሕዝብ ላይ፡ ንጉሥ አድርጎ ቀብቶ አነገሠው። ከእርሱም አብራክ ከወጣው ዘር በመጨረሻው ዘመን ኢየሱስ ክርስቶስ ተወልዶ ዓለሙን እንደሚያድን መንግሥቱንም ዘለዓለማዊ አድርጎ እንደሚያጸናለት ቃል ኪዳን ገባለት።
የእግዚአብሔር አገልጋይ የኾነው ይኽው ዳዊት ኢትዮጵያዊውን ታማኝ ወታደሩን፡ ኦርዮንን በግፍ በማስገደል የሠራውን እጅግ ከባድ ኃጢአት በእውነተኛ ንስሓ ካነጻ በኋላ የሟቹን ኢትዮጵያዊት ሚስቱን ቤትሳባን አግብቶ ሰሎሞንን ወለደ፤ ልጁ ሰሎሞንም ከኢትዮጵያዊቷ ንግሥት ከማክዳ / ከሣባ ቀዳማዊ ምኒልክን ወለደ።
ከዚህ የተነሣ የእሥራኤል የኾነው ሃይማኖታዊውና ምግባራዊው ሥርዓታዊውና ባህላዊው ውርስና ቅርስ ብቻ ሳይኾን እግዚአብሔር ለዳዊት የሰጠው ቃል ኪዳኑንና የቃል ኪዳኑ ዘር ጭምር ለኢትዮጵያና ለኢትዮጵያውያን ኾኑ።
ዳዊትና የእግዚአብሔር መንግሥት ከእርሱ ከዳዊት ዘር ከተገኘችው ከድንግል ማርያም በተወለደው በኢየሱስ ክርስቶስ ንጉሥነትና በርሷ በቅድስት እናቱ ንግሥትነት ለዘለዓለም ጸንታ የምትኖርለት በመኾኑ ፈጣሪው ቃል ኪዳን ገባለት። ” (‘ ኢትዮጵያ እና ኢትዮጵያዊነት ‘ 3 ኛ መጽሐፍ )
ይህን የንቡረ እድ ኤርምያስ ጽሑፍ ከማንበቤ በፊት የክርስቶስ አመጣጥ ኢትዮጵያው ሊሆን እንደሚችል፡ ልክ እንደ ብዙዎች ኢትዮጵያውያን ፡ በውስጤ ይታወቀኝ ነበር። ታዲያ በጣም የሚገርመኝ፣ ግራ አጋብቶ የሚረብሸኝና የሚያበሳጨኝ አንድ ነገር ቢኖር፣ እኛ ኢትዮጵያውያን ይህን የመሰለ ኃብታም ታሪክ፣ ይህን ዓይነት ተወዳዳሪ – የለሽ ታላቅ ጸጋ ተሰጥቶን እንዴት ዋጋ በሌለውና ዓለማዊ በሆነው ቆሻሻ ሁሉ በቀላሉ ልንበላሽ ቻልን ? የሚለው ጥያቄ ነው።
ኔልሰን ማንዴላ የሕይወት ታሪካቸውን በሚያበሥረው መጽሐፋቸው፤ የነጮቹን የአፓርታይድ ሥርዓት ለመዋጋት አንድ ጊዜ ለስብሰባ ወደ አዲስ አበባ በኢትዮጵያ አየር መንገድ ሲበሩ ኢትዮጵያውያን ፓይለቶችን ዓይተው፡ “ እንዴ ! ጥቁር አውሮፕላን አብራሪዎችም አሉ እንዴ ? እንዴት ሊሆን ቻለ ?” የሚለውን ጥያቄ ከአድናቆት ጋር መጠየቃቸውን እናስታውሳለን።
እካሁን ድረስ ከነጮች የዘር አድሎ ሥርዓት መላቀቅ የተሳናቸው አፍሪቃዊ – አሜሪካውያን፡ እዚህ እናንብብ ፡ ኢትዮጵያን የመጎብኘት አጋጣሚ ሲያገኙ፡ በቅድሚያ የሚደነቁበት / የሚገረሙበት አንድ ትልቅ ነገር ቢኖር፡ የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስን፣ የእመቤታችንን የቅድስት ማርያምን እንዲሁም የቅዱሳንን እና የመላእክትን በኢትዮጵያዊና በጥቁር መልክ ተመስለው በየዓብያተክርስቲያናቱ ለማየት መብቃታቸውን ነው። “ ጥቁር እየሱስ ለመጀመሪያ ጊዜ ያየሁት ኢትዮጵያ ውስጥ ነው !” በማለት አንድ ታዋቂ አፍሪቃዊ – አሜሪካዊ ምሁር በኩራት ሲናገሩ አንድጊዜ ሰምቼ ነበር።
ታዲያ አሁን ሁላችንም፡ በተለይ በዚህ የጾም ጊዜ አጥብቀን ልናስብበትና ልንጠየቀው የሚገባን ጥያቄ፦
ለምንድን ነው በአገራችን፡ ብሎንድ / ወርቃማ ጸጉርና ሰማያዊ ዓይኖች ያሏቸው ወይም ፈረንጆችን የመሳስሉ የ ኢየሱስ ክርስቶስ፣ የቅድስት ማርያምና የቅዱሳን ምስሎች በየቦታው ተሠራጭተው የሚታዩት ? የቅዱስ ላሊበላ ዓብያተ ክርስቲያናት እንኳን አልተረፉም !
ፈረንጆቹ እራሳቸውን የመሰለውን የኢየሱስ ክርስቶስ ስዕል ቢስሉ ምንም አይደለም፤ እኛ ግን እንዴት ? ለምን ? ከፈረንጆቹ አስቀድመን ክርስትናን የተቀበለን ሕዝቦች አይደለንምን ? ኢየሱስ ክርስቶስ እና ቅድስት ማርያም ኢትዮጵያዊ አመጣጥ እንዳላቸው እናውቃለን፡ አባቶቻችንም በስዕሎቻቸው ሁሉ የኢትዮጵያውያኑን ገጽታ እንዲይዙ አድርገው ነበር ሲስሏቸው የነበሩት፡ ታዲያ አሁን እኛ ቅዱሳኑን ምን ነክቶን ነው ፈረንጆች ልናደርጋቸው የበቃነው ?
ዲያብሎስ አታልሎ ወደ ወገኖቹ ካልወሰደን በቀር፡ ምንም ሳይቸግረን፣ ምንም ሳይጎድለን እንዴት ከፈረንጆቹ የማይጠቅመውን ነገር ብቻ መርጠን በመቀበል መጪውን ትውልድ፡ ለአእምሮ ከንቱነት እና ለመንፈሣዊ ባርነት ልናጋልጥ ፈቀድን ? ይህ በጣም የሚከነክንና የሚያስቆጣ ድርጊት ነው። ከአባቶቻችን የተረከብነውን ውድ ፀጋ፡ የነርሱን አደራ መንከባከብ ከባድ ሆኖ ስለምናገኘው፡ ታሪክ ዋጋ እንደሌለው፣ የአባቶችንን ሥራ ማውሳቱ ፍሬቢስነት እንደሆነ አድርገን እራሳችንን በማሳማን ቀላል የሆነውን የክህደት መንገድ መርጠን ለባዕዳውያኑ አላፊ “ ሥልጣኔ ‘ በስንፍናችን እንጋለጣለን። በብልጭልጩ ዓይናችን ታውሯልና። ለአባቶቻችን ከአምላክ የተሰጠውን ሥርዓት መናቅ፥ ከእግዚአብሔር የተገኘውን የአባቶቹን ሃይማኖት መተው፥ ትውልዱ፡ አባቶቼ ያቆዩልኝ ትክክል አይደለም፡ የፈረንጁ ትክክል ነው በማለት ነገሮችን ሳይመረመር የማያውቀው ወጥመድ ውስጥ ይገባል። ክርስቶስን በ ጣዖት ፥ ተዋሕዶን በተሃድሶ ፥ ቤተ መቅደስን በቢራ ቤት ፥ መስቀልን በ ፎቅ ፥ ጠበልን በመርዝ ፥ ጥቁርን በ ነጭ ፥ መከዳን በ ሞኒካ ፥ ግዕዝን በላቲን ፥ ነጠላን በ ከረባት ፥ እንጀራን በ ሃምበርገር ፥ እርጎውን በ ኮካኮላ፥ ንጹሑን አየር በመኪና ጭስ በመተካት ምን የሚጠቅመንና የተሻለ ነገር ያገኘን እየመሰለን ይሆን ? ለመደንቆር ፥ ልፍስፍስ ለመሆን፥ ለመታመም እና እራቁት ለመቅረት ካልሆነ በቀር !
ግድየለሽነታችን፡ ከኔ ጀመሮ፡ እጅግ በጣም የሚገርም ክስተት ነው። ሌላው ቢቀር፡ ሥጋዊነት ወይም አካላዊነት የሌላቸው መላእክት እንኳን በነጮች ምስል እኮ ነው እየቀረቡልን ያሉት። ውጭ አገር የሚኖሩትና ብዙ ነገሮችን በቅርብ ለመታዘብ ዕድሉ ያላቸው አባቶች ሳይቀሩ ነው ኢትዮጵያዊውን ክርስቶስ በመተው የፈረንጆቹን ክርስቶስ ደረታቸው ላይ አንጠልጥለው የሚታዩት። ይህ መቸም በመጥፎ ታስቦ ሳይሆን ሌላውን በማክበርና በመውደድ ከመጣ በጎነት የመነጨ ነው። ይህ ተግባር ግን በዚህች በአሁኗ ዓለማችን ከፍተኛ ስህተት ነው ሊሆን የሚችለው። “ እንደ እባብ ልባሞች እንደ ርግብም የዋሆች ሁኑ ” የሚለውን ቅዱስ ቃል ቸል በማለት።
ይህ ጉዳይ በቀላሉ መወሰድ የለበትም ! “ ምን አለበት ? ልዩነት የለውም !” እየተባለለት መታለፍ ያለበትም ጉዳይ አይደለም። ምስሎችና ምልክቶች እጅግ ከፍተኛ ሚና በሚጫወቱባት ዓለማችን የኢየሱስ ክርስቶስ ምስል ፈረንጅ ወይም አይሁድ እና ኢትዮጵያዊ መምሰል ትልቅ ቦታ፡ ከፍተኛ ዋጋ ይኖረዋል። ምናልባትም ብዙ ኢትዮጵያውያን ኢትዮጵያዊውን ተዋሕዶ እምነታቸውን እየተው ወደ መጤው የፈረንጅ እምነት ከሚወድቁባቸው ምክኒያቶች አንዱ ይህ የአባቶቻችንን ትክክለኛ ኢትዮጵያዊ የሥዕል ጥበበ ባሕል እየተተወ እና እየተበላሸ በመምጣቱ ሊሆን ይችላል። ይህም እየተሠራ ያለው ጥፋት / ኃጢዓት፡ በአንድ በኩል፡ ወደ መንግስተ ሰማይ የሚወስደውን በር በወገኖቻችን ላይ እየዘጋባቸው መሆኑን፡ በሌላ በኩል ደግሞ ሃቁን በመካድ፡ የሌለውን የክርስቶስን፣ የማርያምን እና የቅዱሳንን ማንነት ያለአግባብ ቀስበቀስ እየቀየርን መሆኑን ሊያሳየን ይችላል።
እግዚኦ መኻረነ ክርስቶስ !
የፕሮቴስታንት ሃይማኖት ፓስተር የነበሩት የጀርመን ፌደራል ሪፓብሊክ ርዕሰ ብሔር፡ ዮአኪም ጋውክ፡ ባለፈው ማክሰኞ የላሊበላ ቆይታቸው፡ የእነ ቤተ ጊዮርጊስን ተዓምራት በቦታው ተገኝተው ከታዘቡ በኋል የሚከተለውን በመመሰጥ ተናግረው ነበር፦
“ ኢትዮጵያውያኑ ጽኑ እምነታቸውን በቋጥኙ ቅርጽ ያንጸባርቁታል፡ እዚህ ተገኝቼ ይህን ድንቅ ሥራ በዓይኔ ለማየት ስበቃ የጉዞ ፊልሞች የሚያቀርቧቸው ምስሎች ስሜትን የመቀስቀስ ብቃት እንደሌላቸው አሁን ተገነዘብኩ፡ ላሊበላ በመምጣቴ፡ ይህች ቦታ በርግጥም የሰው ልጅ ዘር ምንጭ መሆኗን ለመገንዘብ በቅቻለሁ፡ ክርስቲያናዊ ስሜቴም ተቀስቅሷል፡ ተደንቄአለሁ። “
አስደናቂ የሕይወት ታሪክ ያላቸው እኚህ ሰው፡ በኮሙኒስቷ ጀርመን ( ቻንስለሯም ከዛው ናቸው ) በፕሮቴስታንት ፓስተርነት የሃይማኖት ጠላት ከነበረው የምስራቅ ጀርመን መንግሥት ጋር እየተፋለሙ ነበር ሲኖሩ የነበሩት። አዲስ አበባ እንደገቡም የፕሮቴስታንቶችን የመቃብር ቦታ በቅድሚያ ለመጎብኘት መሻታቸው ከዚህ ታሪካቸው ጋር የተያያዘ በመሆኑ ሊሆን ይችላል። ጀርመኖች፡ ግማሹ ካቶሊክ ግማሹ ፕሮቴስታንት ናቸው። በማርቲን ሉተር የተጀመረው የፕሮቴስታንቶች ተሃድሷዊ እንቅስቃሴ መሠረቱ ጀርመን እንደመሆኑ፤ ይህ እንቅስቃሴ ክርስቲያናዊ ሕይወትን አስመልክቶ የትኛውን መንገድ እንደተከተለና ምን ዓይነት ውጤት እንዳመጣ ፕሬዚደንቱም፡ እውነተኛ የሆኑ ጀርመናውያንም ያውቁታል። እንቅስቃሴው ባጭር ጊዜ ውስጥ (500 ዓመት አይሞላም ) ክርስቲያናዊ ሕይወትን / ክርስትናን ከሕብረተሰቡ ለማጥፋት በቅቷል፡ ሕዝቡን ከፍተኛ መንፈሳዊ ውድቀት ላይ ጥሎታል። “ ከፍሬያቸው ታውቋቸዋላችሁ። ከእሾህ ወይን ከኩርንችትስ በለስ ይለቀማልን ?” ፕሬዚደንቱም በላሊበላዋ አጭር ቆይታቸው ይህን የተገነዘቡ መሰለኝ።
በብዙ አውሮፓውያን ሕዝቦች ዘንድ “ ጥቁር ማዶና ” ወይም “ ጥቁር ማርያም ” ተብላ የምትጠራዋ እመቤታችን ከፍተኛ አክብሮት እንዳላት ይታወቃል። ከፊሊፒንስ አገር እስከ ፖላንድና ሜክሲኮ ድረስ በመላው ምድራችን ብዛት ያላቸው የክርስትና እምነት ተከታዮች ጥቁሯ ማዶና የሚሏትን ኢትዮጵያዊቷን ጽዮን ማርያምን በጥልቁ ማክበር ልዩ መለያቸው ከሆነ ብዙ ዘመናት አሳልፏል።
ከ 11 ኛው እስከ 13 ኛው ምዕተዓመት ባለው ጊዜ ወደ ኢትዮጵያ ተጉዘው እንደነበር የሚነገርላቸው፡ ናይትስ ኦፍ ቴምፕላርስ ፡ የጥቁሯ ማዶናን ምስጢር ከኢትዮጵያ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን አግኝተው ወደ አውሮፓ፡ በተለይ ወደ ፈረንሳይ ይዘው በመሄድ ለአብዛኞቹ አውሮፓውያን እንዳስተዋወቋቸው የሚዘክር ታሪክ አለ። አንዴ ንግሥት ሣባ ሌላ ጊዜ ደግሞ ማርያ ማግዴላ ነች ይሏታል። የተዋሕዶ ክርስትና ተከታዮች፡ እመቤታችን ማርያምን የ “ ብርሃን እናት ” ብለው ስለሚጠሯት እንዲሁም ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በ ብርሃንና በ ፀሐይ ስለሚመሰል፡ ቴምፕላሮቹም ይህን የጽኑ እምነት መግለጫ ከኢትዮጵያ ወስደው በጨለማ ውስጥ ለነበሩት አውሮፓውያን አድርሰው ይሆናል የሚል ሃሳብ አለ። መቼም እውነትን – ደባቂዎቹ አውሮፓውያን ባለ ታሪኮች ለሁሉም ነገር የቴምፕላሮችን ስም እያነሱ ያልተፈጸመውን ሁሉ ተጽፍሞ ይሆናል በማለት ታሪክን ማበላሸት ይቀናቸዋልና፡ መንፈሳዊ ተሰጥኦ ያላቸው አውሮፓውያን በራዕይ ኢትዮጵያዊቷ ጽዮን ማርያምን ለማየት አልተቻላቸውም፡ ቴምፕላሮች ናቸው ምስሏን ከኢትዮጵያ ይዘውት የመጡት ብለው ይናገራሉ። የላሊበላን ዓብያተ ክርስቲያናት እነዚሁ ቴምፕላሮች ናቸው የሠሯቸው፡ ኢትዮጵያውያን ለዚህ ብቃት የላቸውም እስከ ማለት ደርሰው የለም። ከኛም መኻል ይህን ቅሌታማ የፈጠራ ወሬ የሚያስተጋቡ አሳፋሪዎች አልጠፉም።
ምስጢሩ ግን፡ ኢትዮጵያዊቷ እመቤታችን በመንፈስ ድኻ ለሆኑት የዓለማችን ነዋሪዎች በራዕይ እየተገለጠችላቸው ነው። ማንነቷንም ባለመደበቋ፡ ለአሕዛቡ ሁሉ ጠቆር ብላ ስለታየቻቸው ጥቁር ማዶና የሚል ስም ሰጥቷል። በፓላንድ እና በ ክሮኤሺያ የሚገኙት ጥቁር ማዶናዎች ንግሥት ማከዳን / ሣባን እንደሚያስታውሷቸው፡ በርሷም በኩል በየአገሩ ተዓምራተ ማርያምን በየጊዜው በማየታቸውና እመቤታችንንም በማክበር ህይወታቸውን በጥሩ መልክ ለመለወጥ እንደበቁ ብዙ መረጃዎች ይመሰክራሉ። አብዛኛው ዓለም ግን ይህን ምስጢር ላለማውጣት እስካሁን ድረስ አፍኖ ይዞታል። ኢትዮጵያዊ ዝርያ አለባት የምትባለዋ ( እንዳለባት በጣም እጠረጥራለሁ ) የታላቋ ብሪታንያ ንግሥት ኤልሣቤጥ እንኳ፡ ትክክለኛው ማንነቷ እንዳይታወቅባት ያው አፍና እንድትኖር ተገድዳለች። አንጋፋዎቹ ሩሲያዊው አሌክሳንደር ፑሽኪን ፣ እንግሊዛዊው ሰር ፒተር ኡስቲኖቭ በኢትዮጵያዊው አመጣጣቸው ይኮሩ ነበር።
በፖላንዷ ቼስቶኾቫ ( Częstochowa ) የምትገኘው ጥቁሯ ማዶና በአገሬው ሕዝብ ዘንድ ከማንም በላይ ከፍተኛ አክብሮት ያላት፣ በብዙ መቶ ሺህ የሚቆጠሩ ጎብኝዎችን በየሣምንቱ የምትስብ፣ ለናዚዝምና ኮሙኒዝም ውድቀት ከፍተኛ አስተዋጽዖ ያበረከተች፣ የፖላንድ ጥብቅ የካቶሊክ እምነት መሠረት የሆነች፡ እንዲሁም የሮማውን ጳጳስ፡ ዮሐንስ – ጳዎሎስ ሁለተኛውን፡ ካርዲናል ቮይቲላን ያፈለቀች ድንቅ ቦታ ነች። በ ቼስቶኾቫ የሚገኘው የእመቤታችን ምስል በሐዋርያው ቅዱስ ሉቃስ የተሳለ እንደሆነ ይነገርለታል።
ይህ ሁሉ ምንን ያሳየናል ? አዎ ! የንግሥታችን ሣባ ዘር የሆነችው እመቤታችን ቅድስት ማርያም ብርሃኗን ከአገራችን ከኢትዮጵያ እያፈነጠቀች መንፈሣዊ ጨለማ ወደሰፈነባቸው ሩቅ አገራት፡ ቦታና ጊዜ ሳይወስናት ለዘመናት ተዓምር በመሥራት ላይ እንደምትገኝ ነው። መዳን የሚፈልጉትም የርሷን ብዙ ተዓምራት እያዩ በጌታችንና መድኃኒታችን ዓማካይነት ለመዳን መብቃታቸውን ነው። እመቤታችንን ከድተው የነበሩት በዙ ፕሮቴስታንቶች እንኳ ቀስ በቀስ ወደርሷ በመመለስ ላይ ይገኛሉ። የወደቁት ወገኖቻችንም ይህ እድል ይድረሳቸው።
ይህ አሜሪካን አገር በመታየት ላይ ያለው የመጽሐፍ ቅዱስ ፊልም ብዙ ተመልካቾችን ሊስብ መብቃቱ የሚያሳየን፡ የምዕራቡ ዓለም ሰው ወደ መንፈሳዊነት፡ ወደ ክርስትና ሕይወት ለመመለስ ከፍተኛ ፍላጎት እንዳለው ነው። አሁን የምንገኝበት ዘመን በክርስቶስ ላይ፡ በክርስትና ላይ ኃይለኛ ዘመቻ የሚካሄድበት ዘመን እንደመሆኑ፡ የደከመውንና የተበላሸውን ዓለም እንደገና ለማደስ ከማንኛውም ሃይማኖት ይልቅ የኢትዮጵያ ቤተክርስቲያን ተቀዳሚ ሚና የመጫወት እድል አላት። ክርስቶስ በድንጋይ ላይ ሠርቶ ያቆያት ቤት ናትና። የእመቤታችንን ተዓምራት፣ የርሷን አማላጅነት ለማየት፡ የኢትዮጵያ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን ተንከባክባ ያቆየቻቸውን ምስጢራት እና ሥርዓት ለመካፈል በጣም የጓጉ ሕዝቦች አሉ። ለተጨማሪ መረጃ እዚህ ፣ እዚህ እና እዚህ እንመልከት።
“ ኃይሉም ይበረታል፥ ነገር ግን በራሱ ኃይል አይደለም፤ በድንቅም ያጠፋል፥ ያደርግማል፥ ይከናወንማል፤ ኃያላንንና የቅዱሳንን ሕዝብ ያጠፋል። በመታለሉ ተንኰልን በእጁ ያከናውናል፤ በልቡም ይታበያል፥ ታምነውም የሚኖሩትን ብዙዎችን ያጠፋል፤ በአለቆቹም አለቃ ላይ ይቋቋማል፤ ያለ እጅም ይሰበራል። የተነገረውም የማታውና የጥዋቱ ራእይ እውነተኛ ነው፤ ነገር ግን ከብዙ ዘመን በኋላ ስለሚሆን ራእዩን ዝጋ። ” [ ትንቢተ ዳንኤል ምዕራፍ 8 ፥ 24-26]
__
Like this: Like Loading...