😇 ቅዱስ ዮሐንስ መጥምቅ፡ የአዲስ ዘመን ምልክት
በኦርቶዶክሳዊት ቤተክርስቲያን የበዓላት ቀኖና መሰረት የአዲስ ዓመት ዘመን መለወጫ በዓል የቅዱስ ዮሐንስ መጥምቅ በዓል ነው፡፡ ለዚህም ምክንያቱ ቅዱስ ዮሐንስ የአሮጌ (ብሉይ) ዘመን ማብቃት ብስራት፣ የአዲስ ዘመን መምጣት ማሳያ ሆኖ በቅዱሳት መጻሕፍት ስለሚታወቅ ነው፡፡ መጥምቀ መለኮት ቅዱስ ዮሐንስ ብሉይ ኪዳንና በሐዲስ ኪዳን መካከል ከነበሩት ቅዱሳን አበው አንዱ የሆነ፣ ከነቢያት እነ ነቢዩ ኢሳይያስ፣ ከመላእክት ቅዱስ ገብርኤልና ከካህናት አባቱ ዘካርያስ ትንቢት የተናገሩለት ነቢይና ሐዋርያ ነው፡፡ ገና ከሕፃንነቱ ጀምሮ ቅኑት እንደ ገበሬ፣ ጽሙድ እንደ በሬ ሆኖ እግዚአብሔርን ያገለገለ፣ በፍጹም ልቡ ዓለምን የናቀ፣ ከተድላዋና ከደስታዋም የተለየ፣ አምላክን ለማጥመቅ የታደለ ሐዋርያ፣ መምህር፣ ሰማዕት፣ ባሕታዊ፣ ነቢይ፣ ጻድቅ ነው፡፡
😇 የቅዱስ ዮሐንስ መዓርጋት
ቅዱስ ዮሐንስ በርካታ መዓርጋት አሉት፤ የተወሰኑትን ቀጥለን እንመለከታለን፤
- ❖ መጥምቅ /መጥምቀ መለኮት/፡– ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስን በማጥመቁ
- ❖ ነቢይ ከእኔ በፊት የነበረውና ከእኔ የሚበልጠው ይመጣል ብሎ ትንቢት በመናገሩ
- ❖ ካህን ሕዝቡን በማጥመቁ
- ❖ ወንጌላዊ ያስተማረው ትምህርት እንደነቢያቱ ይመጣል ይወለዳል ብቻ ሳይሆን መጥቷል፣ ተወልዷል፣ እነሆ በመካከላችሁ ቆሟል የሚል ለመሆኑ፤ እንደ ነቢያቱ ለቅጣት ምርኮን፣ ለስጦታ /ደስታ/ ምድረ ከነዓንን ሳይሆን ለቅጣት የዘለዓለም ሕይወትን፤ ለስጦታ መንግሥተ ሰማያትንና ገሃነመ እሳትን ማስተማሩ፤ የሥነ ምግባር ትምህርቱም እንደ ወንጌል ትሩፋትን የሚሰብክ በመሆኑ
ርእሰ ዓውደ ዓመት ቅዱስ ዮሐንስ መጥምቅ በብሉይ ኪዳን እና በሐዲስ ኪዳን መሸጋገሪያ ላይ የነበረ ነቢይ በመሆኑ የዓመቱ መጀመሪያና የዘመን መለወጫ በዓል በሆነው መስከረም አንድ ቀን የእርሱ መታሰቢያ እንዲደረግበት፣ በዓሉም «ቅዱስ ዮሐንስ» ተብሎ እንዲጠራ አባቶቻችን ወስነዋል፡፡ ቅዱስ ያሬድም በድጓው «ውስተ ርእሰ ዓውደ ዓመት ተጽሕፈ ተዝካርከ፤ ባርከኒ እንሣእ በረከተከ»፤ «መታሰቢያህ በርእሰ ዓውደ ዓመት ተጻፈ፤ በረከትህን አገኝ /እውሰድ/ ዘንድ «ባርከኝ» ብሎ ምሥጋናና ጸሎት ደርሷል፡፡
ከዚሁ ጋር በተያያዘ መልክአ ዮሐንስ ደግሞ «ርእሰ ዓውደ ዓመት ዮሐንስ ወላዴ መጥቅዕ ወአበቅቴ» ይለዋል /ሠላም ለሥዕርተ ርእስከ/፡፡ «የመጥቅዕ እና የአበቅቴ ወላጅ፣ አስገኚ» ማለት ነው፡፡ ይህም ስም የተሰጠው የዓመቱ ክብረ በዓላት የሚውሉባቸው ቀናትና ዕለታትን ለማስላት የሚጠቅሙት መጥቅዕ እና አበቅቴ የሚባሉት ቁጥሮች በዚሁ በመስከረም አንድ ቀን ስለሚወጡ /ስለሚስሉ/ ነው፡፡
❖ ሰማእት /ምስክር/፡– ስለጌታችን አምላክነትና መድኃኒትነት እንዲሁም ስለ እውነት ስለመሰከረ፤ በመጨረሻም በአላውያን ነገሠታት እጅ ስለ ተገደለ፡፡
ከእነዚህ ሁሉ ስሞች የሚበልጠው ግን መጥምቅ /መጥምቀ መለኮት/ የሚለው ነው፡፡ ምክንያቱም ቅዱስ ዮሐንስ ካደረጋቸውና ከሆናቸው ነገሮች ሁሉ የሚበልጠው አምላክን ማጥመቁ ነው፡፡ ጌታችንም ስለ እርሱ ክብር በተነገረ ጊዜ «እውነት እላችኋለሁ፤ ሴቶች ከወለዱአቸው ወገን ከመጥምቁ ዮሐንስ የሚበልጥ አልተነሣም…» በማለት ይህንን ስያሜ አጽድቆለታል፡፡
😇 ቅዱስ ዮሐንስ መጥምቅ ለእኛ
ቅዱስ ዮሐንስ በዘመኑ የነበሩ ሰዎችን ገሥጾና አስተምሮ ወደ እግዚአብሔር አቅርቧቸዋል፡፡ እኛስ በዚህ ዘመን ያለን ሰዎች ከእርሱ ምን እንጠቀማለን? ሁለት ነገሮችን መጥቀስ ይቻላል፡፡
- ፩. ያስተምረናል፡፡
- ፪. ያማልደናል፡፡
፩. ቅዱስ ዮሐንስ መጥምቅ ያስተምረናል
ቅዱስ ዮሐንስ መጥምቅ በቃሉ /በስብከቱ/፣ በሕይወቱ እና በአገልግሎቱ ዛሬ ድረስ ያስተምረናል፡፡
❖ ሀ. በስብከቱ /በቃሉ/ ያስተምረናል
አንድ ሰው የድኅነትን ጸጋ /ስጦታ/ ከእግዚአብሔር ዘንድ ለመቀበል ሦስት ነገሮች ያስፈልጉታል፡፡ እነዚህም እምነት፣ ምሥጢራትን መካፈል እና ምግባር ናቸው፡፡ ቅዱስ ዮሐንስ በእነዚህ በሦስቱም ዙሪያ ትምህርቶችን ያስተምረናል፡፡
እምነት፡– ቅዱስ ዮሐንስ «አብ ወልድን ይወዳል፤ ሁሉንም ነገር፤ በእጁ ሰጥቶታል፡፡ በወልድ የሚያምን ሁሉ የዘለዓለም ሕይወት አለው፤ በወልድ የማያምን ግን የእግዚአብሔር ቁጣ በእርሱ ላይ ይሆናል እንጂ ሕይወትን አያይም» እያለ ምሥጢረ ን ምሥጢረ ሥጋዌን ያስተምረናል፤ ካላመንም የዘለዓለም ሕይወት እንደሌለን ይነግረናል፡፡
ምስጢራትን መካፈል፡– ቅዱስ ዮሐንስ «መንግሥተ ሰማያት ቀርባለችና ንስሐ ግቡ፡፡»፣ «ከእኔ በኋላ የሚመጣው በመንፈስ ቅዱስ እና በእሳት ያጠምቃችኋል»፣ «የዓለምን ኃጢአት የሚያስወግድ የእግዚአብሔር በግ እነሆ» እያለ ምሥጢራትን /ምስጢረ ጥምቀት፣ ምስጢረ ንስሐን እና ምስጢረ ቁርባንን/ እንድንካፈል ያስተምረናል፡፡
ምግባር፡– «እናንት የእፉኝት ልጆች ለመሆኑ ከሚመጣው ቁጣ እንድታመልጡ ማን መከራችሁ፤ ለንስሐ የሚገባ ፍሬ አፍሩ፤ … እነሆ ምሳር የዛፎችን ሥር ሊቆርጥ ተዘጋጅቷል፤ መልካም ፍሬ የማያፈራ ዛፍ ሁሉ ይቆረጣል፤ ወደ እሳትም ይጣላል፡፡» እያለ ምግባር እንድንሠራ ያስተምረናል፤ ያስጠነቅቀናል።
❖ ለ. በሕይወቱ ያስተምረናል

ከቅዱስ ዮሐንስ መጥምቅ በሕይወቱ እግዚአብሔርን ያስደሰተ፤ «ከሴቶች ከተወለዱ የሚያህለው የለም» የተባለለት ስለሆነ አርአያ ልናደርገው፤ ለዚህ ክብር ያበቃውን ነገር ልንመረምርና በመንገዱ ልንከተለው ይገባናል፡፡ ከሕይወቱ ብዙ ልንማራቸው የሚገቡ ነገሮች ቢኖሩም ጥቂቶቹን ለጊዜው እንመልከት፡–
ትሁት ነው፡– ቅዱስ ዮሐንስ መጥምቅ ጌታ «ከሴቶች ከተወለዱት ወገን የሚያህለው የለም» እያለ ቢያመሰግነውም እርሱ ግን ያሉትን መልካምና ታላላቅ ነገሮች በሙሉ ችላ ብሎ «እኔ የጫማውን ማሰሪያ ልፈታ የማይገባኝ ነኝ» ይል ነበር፡፡ በዚህም ምክንያት ቅዱስ ያሬድ «ዘወጠነዝ ትርሢተ ክብር ትሕትና ወፍቅር ትሕትና ወፍቅር ርእዮ እበዩ ለዮሐንስ…» እያለ የቅዱስ ዮሐንስ የክብሩ ጌጥ፣ የታላቅነቱ ምንጭ ትሕትናው እና እግዚአብሔርን ማክበሩ መሆኑን ይገልጻል፡፡ እመቤታችን በጸሎቷ «ትሁታንን ግን ከፍ ከፍ አደረጋቸው» [ሉቃ.፩፥፶፪] እንዳለችው እርሱ ትሁት ሲሆን እግዚአብሔር ከሁሉ በላይ አከበረው፡፡ የቅዱስ ዮሐንስ ትሕትና ግን ምንጩ ምንድን ነው?
ትሕትና ማለት ምንም ነገር የሌለው መሆን ማለት አይደለም፡፡ እግዚአብሔር በባሕርይው ትሁት ነው፡፡ ጌታ «ከእኔ ተማሩ፣ እኔ ትሁት ነኝ» ይላል፡፡ የእግዚአብሔር ትሕትና ምንጩ ክቡር፣ ባዕለ ጸጋ መሆኑ ነው፡፡ የቅዱስ ዮሐንስ ትሕትና ምንጭም ይኸው ነው፤ በእምነትና በምግባር ያጌጠ ባለ ብዙ ፍሬ ባለ ጸጋ መሆኑ ማንም ትሕትናን የሚፈልጋት ቢኖርም ማድረግ ያለበት ይህንኑ ነው፤ ባለብዙ ምግባር፤ ባለ ትልቅ እምነት መሆኑ፤ ያን ጊዜ ትሕትናው አብሮ ይመጣል፡፡
ሁለተኛው የቅዱስ ዮሐንስ መጥምቅ ትሕትና ምንጭ የእግዚአብሔርን ማንነትና ባሕርይ በሚገባ ማወቁ፤ የራሱን ማንነቱንና አቅሙንም መረዳቱ ነው፡፡ እኛም ትሕትናን ገንዘብ ልናደርግ ብንወድ የእግዚአብሔርን ማንነት፣ ባሕርይ፣ እና ክብር የተቻለንን ያህል ለማወቅ መጣር፤ ራሳችንንም ዘወትር መመርመር፣ ድካማችንን መረዳትና ይህንንም ደግመን ደጋግመን ለራሳችን መንገር አለብን፡፡
ጸጋውን ተጠቅሞ ፍሬ አፍርቷል፡ – ቅዱስ ዮሐንስ በእናቱ ማኅፀን ሳለ መንፈስ ቅዱስ መልቶበት ነበር፡፡ እርሱም ይህንን ጸጋውን አትርፎበታል፤ሕዝቡም ካህናቱም አመጸኞች በነበሩበት በዚያ አስከፊ ዘመን [ሐዋ.፭÷፴፡፴፱] ጻድቅ ሆኖ ተገኝቷል፤ ለራሱ ብቻ ሳይሆን ለሌሎችም በረከት ሆኖ ነበር፡፡ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ሺኖዳ እንዳሉት ለዚህ የበቃው «የበረሃ እና የተራሮች ልጅ» በመሆኑና በብህትውና /በብቸኝነትና/ እና በትህርምት በመኖሩ ነው፡፡
እያንዳንዳችን ከጥምቀታችን ቀጥሎ በሚፈጸምልን ምሥጢረ ሜሮን አማካኝነት መንፈስ ቅዱስ ያድርብናል፡፡ ይህንን ተጠቅመን ሥራ ለመሥራት እኛም እንደ መጥምቁ የራሳችን በረሃ ያስፈልገናል፤ በትህርምትና ራስን በመግዛት መኖር አለብን፡፡
ይህንን ማድረግ የሚገባቸውና የሚችሉት በገዳም ያሉ ሰዎች ብቻ አይደሉም፡፡ በዓለም የምንኖር ሰዎችም ብቻችንን የምንሆንበትና በጸሎት፣ በተመስጦ፣ ቅዱሳት መጻሕፍትን በማንበብ፣ ራሳችንን በመመርመር የምናሳልፈው ጊዜ በመመደብ ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ በወጣትነት ዘመኑ እንዳደረገው መኖሪያ ቤቶቻችንን ገዳማት ማድረግ እንችላለን፡፡ ሁኔታዎችን እያመቻቸን ወደተለያዩ ገዳማት እየሄድን ጊዜ ማሳለፍም ጠቃሚ ነው፡፡
ከዚህም በተጨማሪ ምግባችንን፣ መጠጣችንን እና ልብሳችንን በልክ እያደረግን መጥምቁን ባለ ብዙ ፍሬ በሆነበት ጎዳናው ልንከተለው ያገባናል፡፡
በአግልግሎቱ ያስተምረናል፡ –ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ሺኖዳ ከቅዱስ ዮሐንስ መጥምቅ አገልግሎት ልንማራቸው የሚገቡ በርካታ ቁም ነገሮች አሉ በማለት የሚከተሉትን ይዘረዝራሉ፡፡
ቅድስ ዮሐንስ ያገለገለው ለአጭር /ከስድስት ወራት ብዙ ላልበለጠ/ ጊዜ ብቻ ቢሆንም በርካታ ሥራዎችን ሠርቶ አልፏል፡፡ እኛም አገልግሎታችንን ልንመዝነው የሚገባን በርዝመቱ ሳይሆን በጥልቀቱ፣ በውጤታማነቱ፣ በሚያፈራው ፍሬ እና በሚያመጣው ለውጥ ነው፡፡
ቅዱስ ዮሐንስ ሲያገለግል ዓላማው ሰዎችን ከእግዚአብሔር ጋር ማገናኘት እንጂ ሰዎችን በእርሱ ዙሪያ መሰብሰብና መክበር አልነበረም፡፡ ቅዱስ ማቴዎስ በወንጌሉ እንደሚነግረን «ከኢየሩሳሌም፣ ከመላው ይሁዳ፣ በዮርዳኖስ ዙሪያ ባለው ነገር ሁሉ ሰዎች ወደ እርሱ ይጎርፉ ነበር፡፡» [ማቴ.፫፥፭፡፮] እርሱ ግን «እኔ በውኃ ለንስሐ አጠምቃችኋለሁ፤ ከእኔ በኋላ የሚመጣው ግን በመንፈስ ቅዱስና በእሳት ያጠምቃችኋል፡፡» እያለ ሰዎቹ እርሱን እንዲከተሉ ሳይሆን የጌታችንን መምጣት ተስፋ እንዲያደርጉ የሚያደርግ ትምህርት ያስተምራቸው ነበር፡፡ በዚህም ምክንያት የቅዱስ ዮሐንስ ደቀመዛሙርት በኋላ ወደ ቤተ ክርስቲያን ገብተዋል፡፡
የመጀመሪያዎቹ ጌታችንን የተከተሉት ደቀመዛሙርት የዮሐንስ ደቀመዛሙርት ነበሩ፡፡ ስለዚህ በዚህ ዘመን መታጀብ /በሕዝብ መከበብ/ ለሚያስደስተን የእግዚአብሔርን ሳይሆን የእኛን ተከታዮች እንደ ፈሪሳውያን ለምንፈልግ አገልጋዮች ትልቅ ተግሳጽ ነው፡፡
«በማግስቱ ዮሐንስ ከሁለቱ ደቀመዛሙርቱ ጋር እንደገና በእዚያው ቦታ /ጌታችን በተጠመቀበት/ ቦታ ነበር፡፡ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስም በዚያ ሲያልፍ አይቶ «እነሆ የእግዚአብሔር በግ» አለ ሁለቱ ደቀመዛሙርትም ይህን ሲናገር ሰምተው ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስን ተከተሉት» [ዮሐ.፩፥፴፭፡፴፯]
የሐዋርያት ሥራ መጽሐፍም በርካታ የዮሐንስ ደቀመዛሙርት የነበሩና የእርሱን ጥምቀት የተጠመቁ ሰዎች በቀላሉ ወደ ክርስቲያኖች ማኅበር እንደተቀላቀሉ ይነግረናል፡፡ [ሐዋ.፲፰፥፳፬+ ፲፱፣ ፮፥፲፫፡፳፬]

ራሱም ይህንን አቋሙን እንዲህ በማለት ልብ በሚነኩ ቃላት እንዳጋለጠው ወንጌላዊው ዮሐንስ በወንጌሉ መዝግቦታል፡፡
ሰዎች ወደ ቅዱስ ዮሐንስ መጥተው «መምህር፣ በዮርዳኖስ ከአንተ ጋር የነበረው፣ ስለ እርሱም የመሰከርክለት … ሰው ሁሉ ወደ እርሱ እየሄዳ ነው» ባሉት ጊዜ እንዲህ ሲል መለሰ «ከላይ ካልተሰጠው በቀር ማንም አንዳች ሊቀበል አይችልም፡፡ «እኔ ክርስቶስ አይደለሁም፤ ነገር ግን ከእርሱ በፊት ተልኬአለሁ» እንዳልሁ እናንተ ራሳችሁ ትመሰክራላችሁ፡፡ ሙሽራይቱ የሙሽራው ነች፡፡ ድምፁን ለመስማት በአጠገቡ የሚቆመው ሚዜ ግን የሙሽራውን ድምፅ ሲሰማ እጅግ ደስ ይለዋል፤ ያ ደስታ የእኔ ነው፤ እርሱም አሁን ተፈጽሟል፡፡ እርሱ ሊልቅ፤ እኔ ግን ላንስ ይገባል፡፡»
እውነት ነው፡፡ ሙሽራይቱ ቤተ ክርስቲያን የሙሽራው የክርስቶስ ነች፡፡ አገልጋዮች ሚዜ ናቸው፡፡ ሥራቸውም ሙሸራይቱን ወደ ሚዜው ማቅረብ ነው፡፡
ቅዱስ ዮሐንስ ሲያገለግል በድፍረት ነው፡፡ እርሱ በነበረበት ወቅት ሔሮድስ አንቲጳስ የወንድሙን ሚስት አግብቶ የሚገሥጸው ጠፍቶ ነበር፡፡ ቅዱስ ዮሐንስ ግን በበረሃው ሳለ ደፋር፣ ለሰው ፊት የማያደላ፣ መሆንን ተምሮ ነበርና ገብቶ ገሠፀው፡፡
ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ሺኖዳ እንዲህ ይላሉ «ከአገልግሎቱ ሊያዘገየው ወይም ሊያስተጓጉለው የሚችል ቢሆንም እንኳን ተገቢውን ነገር ከማድረግ ወደ ኋላ አላለም፡፡ አስተሳሰቡም እንዲህ ነው «እግዚአብሔር እንዳገለግል ፈቃድ ከሆነ አገለግላለሁ፤ ካልሆነም የእርሱ ፈቃዱ ይሁን፡፡ ዋናው ነገር እውነትን መመስከር ነው» ቅዱስ ዮሐንስ ስለእውነት ራሱን አሳልፎ ቢሰጥም ከሞተ በኋላም ቢሆን የትምህርቱ ድምፅ ሄሮድስን ሲወቅሰው ኑሯል፡፡»
እውነት ነው፡፡ በመጀመሪያ ደረጃ ከሞተ በኋላም ቢሆን ራሱ አስራ አምስት ዓመት ዙራ አስተምራለች፡፡ ሔሮድስም ከሞት ተነሥቶ የሚመጣ እስኪመስለው ድረስ ይፈራው እንደበር ቅዱስ ማቴዎስ በወንጌሉ ጽፏል «በዚያን ጊዜ የአራተኛው ክፍል ገዢ የነበረው ሄሮድስ /አንቲጳስ/ ስለ ኢየሱስ ዝና ሰማ፤ ባለሟሎቹንም እንዲህ ከሆነ መጥምቁ ዮሐንስ ከሞት ተነሥቶ መጥቶአል ማለት ነው፤ ይህ ሁሉ ድንቅ ተዓምራት በእርሱ የሚደረገውም ለዚህ ነው» አላቸው፡፡ [ማቴ.፲፬፥፩፡፪]፡፡
😇 ቅዱስ ዮሐንስ መጥምቅ ያማልደናል
ቅዱስ ዮሐንስ ዛሬ እኛን እግዚአብሔር ለወዳጆቹ በሰጠው ቃል ኪዳን መሠረት በጸሎቱ ከእግዚአብሔር ያማልደናል፡፡
ቤተ ክርስቲያንም ዘወትር «ሰአል ለነ ዮሐንስ» «ዮሐንስ ሆይ ለምንልን»፤ ትለዋለች፤ «በአንተ ዮሐንስ መጥምቅ መሐረነ» «ስለ ዮሐንስ ስትል ማረን» እያለችም ትጸልያለች፡፡ እኛም ገድሉንና፣ መልኩን በመጸለይ፣ መታሰቢያው በሚደረግበት ጊዜም በስሙ ዝክር በመዘከር፣ ቸርነት በማድረግ በረከትን ለማግኘት ልንተጋ ይገባናል፡፡
«ማንም ከእነዚህ ከታናናሾቹ ለአንዱ ቀዝቃዛ ውኃ ብቻ በደቀመዛሙርቶቼ ስም ቢያጠጣ፤ እውነት እላችኋለሁ ዋጋው አይጠፋበትም» [ማቴ.፲÷፵፪]
«የቅዱስ ዮሐንስ ጸሎቱና በረከቱ ይደርብን! አማላጅነቱ ይደረግልን»
ወስብሐት ለእግዚአብሔር
______________