እንደ ነቢዩ ሙሴ በቅዱሳን ስም በገባላቸው ቃል ኪዳንና መሀላ በማሳሰብ ምህረትን ልንለምን ይገባናል በተለይም አምላክን በወለደች ከፍጡራን ሁሉ በላይ በሆነች በቅድስት ድንግል ማርያም ኪዳነ ምህረት የይቅርታ ውል ስምምነት በተደረገባት የምህረት መፍሰሻ በሆነች በእመቤታችን ስም ብንለምን አምላክ ምህረትና ይቅርታን ያደርግልና የመዳናችን ምልክት ትሆነን ዘንድ ድንግል ማርያምን የሰጠን አምላክ ምስጋና ይድረሰው አሜን፡፡
ኪዳነ ምሕረት ስንል የምህረት ቃልኪዳን ማለት ነው፡፡በዚህ ውስጥም ምህረት አድራጊው ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሲሆን ምህረት ተቀባይም መላው የአዳም ዘር ነው፡፡
እናታችን ቅድስት ድንግል ማርያም በምድራዊ ቆይታዋ ዘውትር ወደ ክርስቶስ መካነ መቃብር ጎለጎታ እየወረደች ትፀልይ ነበር፡፡ ልጇ እና ወዳጇ ጌታችን መድሐኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ያደረገችው ልመናና ፀሎት ተመልክቶና ሰምቶ የምህረት ቃል ኪዳን ገባለት ፡፡
እንኳን የእናቱን ፀሎት እና ልመና ቀርቶ ዘውትር በሀጥያት የምንዘፈቀውን እኛን ክፉዎቹን የሚሰማ አምላክ ስለ አንቺ ፣ ስለ እናቴ ክብርና ፀጋ ስል ይኸው ቃሌ ብሎ ቃልኪዳን አደረገ፡፡
« ከመረጥሁት ጋር ቃል ኪዳኔን አደረግሁ። … » መዝ, 89 : 3 እንዲል መፅሐፉ፡፡
ስሟን ለሚጠሩ፣ በእርሷ አማላጅነት ለሚታመኑ በምድር በረከትን በሰማይ የዘለዓለም መንግስትን እንደሚወርሱ የምህረት እና የቸርነት ቃልኪዳን ሰጥቷታል ፡፡
ታላቁ መፅሐፍ እንዲህ ይላል፦
“. . . ቀስቲቱም በደመና ትሆናለች፤ በእኔና በምድር ላይ በሚኖር ሥጋ ባለው በሕያው ነፍስ ሁሉ መካከል ያለውን የዘላለም ቃል ኪዳን ለማሰብ አያታለሁ። ” ኦሪት ዘፍ. 9 : 16
በዚህም መሠረት ቃልኪዳኗን ምክንያት በማድረግ ኪዳነ-ምህረት እያልን እንጠራታለን!
እንኳን ለ “ኪዳነ ምሕረት” አደረሰን። የእመቤታችን ምህረት እና ረድዔት፤ በረከት ከሁላችን ጋር ይሁን!
❖ ቅድስተ ቅዱሳን
❖ ሰዓሊተ ምሕረት
❖ ተላኪተ እግዚአብሔር ወ ሰብእ
❖ ቤዛዊተ አለም
❖ ኪዳነ ምህረት
❖ ንጽሕይተ ንጽሐን
❖ ድንግል በክልኤ
❖ ድንግል ወእም
❖ ፍጽምተ ሥጋ ወነፍስ
❖ በድንጋሌ ሥጋ በድንጋሌ ነፍስ የፀናች
❖ እመብርሃን
❖ ምልዕተ ጸጋ
❖ እመቤታችን
❖ ወላዲተ አምላክ
________________