እንኳን ለወንጌላዊ ቅዱስ ዮሐንስ በአል አደረሰን
ወንጌላዊው ቅዱስ ዮሐንስ
በዚህች ቀን ወንጌላዊው ቅዱስ ዮሐንስ ሞትን ሳይቀምስ የተሰወረበት ቀን ነው፤ ዮሐ ፳፩፥፳
ዮሐንስ ማለት ” የእግዚአብሔር ጸጋ ነዉ“፤ ደስታ ማለት ነዉ፡፡ አባቱ ዘብዴዮስ ፤ እናቱ ማርያም ባዉፍልያ ትባላለች፡፡ቁጥሩ ከዐሥራ ሁለቱ ሐዋርያት የሆነ ያዕቆብ የተባለ ወንድም ነበረዉ፡፡ ማቴ ፬፥፳፩ ማር ፩፥፳ ፤ ማቴ ፳፥፳ ቅዱስ ዮሐንስ አስቀድሞ የዮሐንስ መጥምቅም ደቀ መዝሙር ነበር፡፡ ዮሐ ፩፥፴፭ ቅዱስ ዮሐንስ ከአባቱና ከወንድሙ ጋር ዓሣ በሚያጠምድበት በገሊላ ባህር ላይ መረቡን ሲያበጅ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለሐዋርያነት ጠራዉ፡፡ እሱም አባቱን ሌሎቹንና ታንኳን ትቶ ከወንድሙ ያዕቆብ ጋር ጌታን ተከተለዉ፡፡
ቅዱስ ዮሐንስ ብዙ ስሞች አሉት፦
-
👉 ዮሐንስ ወልደ ነጎድጓድ
-
👉 ዮሐንስ ፍቁረ እግዚእ
-
👉 ዮሐንስ ቁጽረ ገጽ
-
👉 ዮሐንስ ታኦሎጎስ
-
👉 ዮሐንስ አቡቀለምሲስ
-
👉 ዮሐንስ ወንጌላዊ
-
👉 ዮሐንስ ዘንስ
ከሐዋርያት መካከል ሞትን ያልቀመሰ በህይወተ ሥጋ እያለ ወደ ሰማይ የተነጠቀ እንደ ሔኖክ ፣እንደ ኤልያስ በብሔረ ሕያዋን የሚኖር ሐዋርያ ነዉ፡፡ጌታችንም ለቅዱስ ጴጥሮስ “”ዮሐንስ እኔ እስክመጣ ድረስ በሕይወት ይኖር ዘንድ ብወድስ ምን አግዶህ??”›ዮሐ ፳፩፥፳ ይህም እስከ ምጽአት ድረስ እንደሚኖር መናገሩ ነዉ፡፡በማቴ 16፡18 ላይ “እዉነት….……ሞትን የማይቀምሱ አንዳንድ አሉ“”›ያለዉ ቃል ለቅዱስ ዮሐንስና መሰሎቹ የተነገረ ቃል ነዉ፡፡
ወንጌላዊ ቅዱስ ዮሐንስ በሃይማኖታዊ ጉዳይ ላይ ምን ያህል ጠንቃቆች መሆን እንደሚገባን ሲናገር፦
“ለሚወጣ ሁሉ በክርስቶስም ትምህርት ለማይኖር ሰው አምላክ የለውም፤ በክርስቶስ ትምህርት ለሚኖር አብና ወልድ አሉት። ማንም ወደ እናንተ ቢመጣ ይህንም ትምህርት ባያመጣ በቤታችሁ አትቀበሉት ሰላምም አትበሉት፤ ሰላም የሚለው ሰው በክፉ ሥራው ይካፈላልና።” [፪ኛ ዮሐ፡ ፱፥፲፩]
በማለት አርቀን እንድናጥርና እንድንጠነቀቅ አስተምሮናል፡፡
የቅዱስ ዮሐንስ ወንጌላዊ በረከቱ ረድኤቱ ከሁላችን ጋር ይሁን፡ ራዕዩ ይገለጥልን!