እንኳን ለበዓለ መስቀል በሰላም ሑላችንንም አደረሰን፡ አደረሳችሁ!!
ቅዱስ መስቀሉ መጋቢት ፲ ቀን ነበር ከተቀበረበት የወጣው። በክርስቶስ ደም የተቀደሰው ይህ ክቡር መስቀል ንግሥት ዕሌኒ መስከረም 16 ቀን 320ዓ.ም በዕጣን ጢስ ምልክት ቁፋሮ አስጀምራ መጋቢት ፲ ቀን አግኝታ በማውጣት ታላቅ ቤተመቅደስ ጎልጎታ ላይ ሠርታ በክብር አስቀመጠችው። ይህ መስቀልም ከዚያ ዕለት ጀምሮ እንደ ፀሐይ እያበራ፣ ድውይ እየፈወሰ፣ አጋንንት እያባረረ፣ ልዩ ልዩ ተአምራት እየሰራ፣ ሙት እያነሳና ዕውር እያበራ ተአምራቱን እስክ ዛሬ ድረስ ቀጠለ።
የመስቀሉን ኃይለኛነት የተገነዘቡት አባቶቻችንና እናቶቻችን፣ ወንድሞቻችንና እኅቶቻችንን በግንባራቸው፣ በአንገታቸውና በእጃቸው ላይ የመስቀል ንቅሳት አድርገው ስናይ በሞኝነትና በግብዝነት እንደ ባላገርነት አድርገን ስንቆጥረው ነበር፤ አውሬው በልጆቹ አድሮ እያታለለን ነበርና፦
“ለክርስቶስ መስቀል ጠላቶች ሆነው ይመላለሳሉና ብዙ ጊዜ ስለ እነሱ አልኋችሁ አሁንም እንኳ እያለቀስኩ እላለሁ መጨረሻቸው ጥፋት ነው ሆዳቸው አምላካቸው ነው ክብራቸው በነውራቸው ነው ሐሳባቸው ምድራዊ ነው” [ፊል. 3፤18-19]
አሁን የንቅሳት ባህል (ለማይጠቅመው ነገር ሁሉ) በመላው ዓለም እንደ ጉድ በተስፋፋበት ዘመን፤ ይህ የመስቀል ንቅሳት ማድረግ ምን ያህል ቆንጆና ብልህነት የተሞላበት ተግባር እንደሆነ እየተገነዘብነው ነው።
ለዘመናት በመሀመዳውያን በከፋ መልክ የሚበደሉት ግብጻውያን ክርስቲያን ወንደሞቻችን እና እህቶቻችን “መስቀሌን ከአንገቴ ቢበጥሱ ከቆዳየ ላይ ግን ፍቀው አያወጡትም” በሚል ጽኑ የክርስቲያናዊ መንፈስ እጆቻቸው ላይ መስቀል ይነቀሳሉ፤ በዚህም ፀረ–ክርስቶስ በዳዮቻቸውን ድል ነስተዋል፤ በዚህም እስከ ዕለተ ሞታቸው ድረስ ክርስቲያን መሆናቸው ተለይተው እንዲታወቁ አድርገዋል። እግዚአብሔር የተመሰገነ ይሁን!
አንዳንድ ማስረጃዎች እንደሚጠቁሙን የግብጻውያኑ የመስቀል ንቅሳት ለመጀመሪያ ጊዜ የተገኘው በስምንተኛው መቶ ክፍለ ዘመን ነበር። በወቅቱ መነኮሳት ነበሩ እጆቻቸውን በክርስትና ምልክቶች ማተም የጀመሩት፤ እነርሱም ይህን የተማሩት ከኢትዮጵያውያን ክርስትያኖች መሆኑ ይታወቃል።
የአውሬውን ምልክት ለመከላከል ይቻለን ዘንድ ሁላችንም በቀኝ እጃችን ወይም በግምባራችን ላይ [ራዕይ 10: 4፤13:16] የመስቀል ንቅሳት የምናደርግበት ዘመን ላይ የደረስን ይመስለኛል።