ዘመነ ስብከት – ሥላሴ
Posted by addisethiopia / አዲስ ኢትዮጵያ on January 15, 2014
በስመአብ ወወልድ ወመንፈሥ ቅዱስ፡ አሐዱ አምላክ፡ አሜን
“ዘመነ ስብከት” በታኅሣሥ ፰ እና በጥር ፲ ቀኖች መካከል ያሉት አራት የእሑድ ሰንበታት ከነሳምንታቶቻቸው፡ እያንዳንዳቸው በቅደም ተከተል
- ስብከት
- ብርሃን
- ኖላዌ
- ጌና
ተብለው የሚጠሩት ናቸው።
በእነዚህ ሰንበታትና ሳምንታት፦
እግዚአብሔር ወልድ በመንፈስ ቅዱስ ግብር በድንግል ማርያም ማሕፀን ተፀንሶ በፍጹም ሰውነት ከእርሷ ስለመወለዱ፡ የሰውነት አመጣጡም ለዓለሙ በደል ቤዛ ኾኖ የመሥዋዕትነት ዋጋን በመክፈል ፍጥረቱን ለማዳን ስለመኾኑ፡ “ኢየሱስ ክርስቶስ” በተባለበት ስሙም በምድር ላይ እየተመላለሰ፡ ከኃጢዓት በቀር እውነተኛውን ሰውኛ አኗኗር በመኖር ለሰው ልጆች ኹሉ ፍጹም አርአያነትን ስለማበርከቱ በነቢያት የተነገሩትን የእግዚአብሔርን ትንቢታዊ ቃላት በመጥቀስ ትምህርትና ምዕዳን (ምክር) ይሰጥባቸዋል፡ የተስፋ ዝማሬ ይሰማባችዋል፡ ስለሥጋዌ ምሥጢርም ይቅኔያት ማዕበል ይወርድባቸዋል።
እነዚህን አርእስት በመከተል “ፈኑ እዲክ እም አምርያም!..ፈኑ ብርሃነከ ወጽድቀከ…” ማለትም፡ “እጅህን ከሰማይ ላክ!.. ብርሃንህንና እውነትህን ላክ!” እያሉ የቀደሙት ሰዎች ወደፈጣሪያቸው ያቀርቡት የነበረው ያልተቋረጠ ልመና ተሰምቶላቸው፡ “እነ ውእቱ፡ ኖላዌ ‘ኔር!’” ማለትም ቸር ጠባቂ እኔ ነኝ!” የሚላቸውና “የእግዚአብሔር ቀኝ እጅ“፡ እውነተኛው የዓለም ብርሃን የተባለው ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ እነሆ “ሰው ኾኖ በድንግል ማሕፀን ተፀነሰ ተወለደ እንደሰው በምድር ላይ ተመላለሰ!” በማለት በመንፈስ ወደኋላ ተመልሰን የነቢያትን የተስፋ ጉዞ ከፈጸምን በኋላ ከጥምቀቱ በዓል እንደርሳለን።
የጥር ሥላሴ
ከበዓለ ጥምቀት በፊት ግን ጥቂት ቀደም ብሎ፡ በጥር ፯ ቀን፡ “የጥር ሥላሴ” በዓል ይከበራል። ይህም የኾነው በታኅሣስ ፩ ቀን በሚውለው በየሱስ ክርስቶስ ትስብእት፡ ማለትም አምላክ ሰው ኾኖ በድንግል ማርያም ማሕፀን በመፀነሱ የእግዚአብሔር የአንድነቱና የሦስትነቱ ምሥጢር ስለተገለጸ፡ ስለታወቀና ስለተረዳ የምስጢረ ሥላሴና የምስጢረ ሥጋዌ ነገር በሰፊው እየተነገረ ትምህርቱ እንዲሰጥበት ምሥጢሩም እንዲፍታታበት ታስቦ ነው።
ምንጭ፦ “ኢትዮጵያ እና ኢትዮጵያዊነት” ኹለተኛ መጽሓፍ
Leave a Reply