አባ ሳሙኤል፡ “መሪና አመራር” በሚለውና በ2003 ዓ.ም የወጣው መጽሐፋቸው የኢትዮጵያ ቤተክርስቲያንን ወቅታዊ ኹኔታ ያገናዘቡ ብልህነት የተሞላባቸውን ነጥቦች ለአንባቢው አቅርበዋል።
ከአድናቆትና ክብር የተሞላበት ምስጋና ጋር ከመጽሐፉ ቀንጨብ አድርጌ የሚከተሉትን ሓሳቦቻቸውን እንሆ አቅርቤአለሁ።
ምናልባት ለቤተክርስቲያናችን መሪነት በእጩነት ከቀረቡት አባቶች መካከል አባ ሳሙኤል አንዱ ከሆኑ የኔን ድምጽ አግኝተዋል።
6ኛውን ፓትርያርክ ለመምረጥ የሚካሄድበት ሣምንት ለእናት ኢትዮጵያ ልዩ ጸሎት የምናደርግበት የ ነነዌ ጾም ወቅት ስለሆነ መንፈስ ቅዱስ ስራውን እንዲሰራ፡ አባቶችንም እንዲረዳ በአንድነት ልባችንን ልናርገበግብ ይገባናል። ኢትዮጵያ የ6ኛውን ፓትርያርክ ፍለጋ በጀመረችበት ወቅት የሮማ ካቶሊክ ጳጳስም 112 ኛውን (100 + 6 + 6) ጳጳስ ለመምረጥ በመዘጋጀት ላይ ትገኛለች። አጋጣሚ? የሮማው መብረቅ፡ የሩሲያው በራሪ ኮከብ ምን እየነገሩን ይሆን? አባታችህ ሔኖክ በመጽሐፉ ላይ “አሁን ጎርፍ ሳይሆን እሳት ነው ከላይ የሚመጣው” ያለን የመጨረሻው ዘምን ደርሶ ይሆን? እግዚአብሔር ይጠብቀን! የሚገርመውና የማይገርመው ግን ሊቃውንቱ አውቀነዋል፣ ዓይተነዋል፣ አግኝተነዋል በማለት ምድራችንን በ20ሺህ ኪሎሜትር ርቀት ዛሬ ማታ እንደሚያልፍ የተነበዩልንን ተለቅ ያለ በራሪ ኮከብ (Meteor > Metéora Eastern Orthodox Monasteries) በኩራት ሲጠባበቁ ይህ ያልታየው ሌላ ኮከብ ሹልክ ብሎ በሩስያ አረፈ። ይህም የሚያሳየው ምንም እውቀት የሌለን ግብዞች መሆናችን ነው። 10% ብቻ የሚሆነውን ነገር በዙሪያችን ማየት እንደምንችል ይህ ሌላ ትልቅ ማስረጃ ነው።
ለማንኛውም፡ ወደ መጽሐፉ፦
እግዚአብሔር አምላክ ታላላቅ ሥራዎችን ለማስፈጸም መሪዎችን እንዲመርጥና በእነርሱም አማካይነት ሥራውን እንደሚያስፈጽም ግልጽ ነው።
የማናቸውንም መሪ ተግባር በግልጽና በቀላል ኹኔታ ለመረዳት አገልግሎትን ለመስጠትና ሓላፊነትን ለመቀበል ዝግጁና ፈቃደኛ መሆንን መሠረት ማድረግ ይጠይቃል።
መሪነት ካለፈው ትውልድ ወደ አዲሱ ትውልድ መተላለፍ አለበት። ይሁን እንጂ የሽግግሩ ሒደት አባት ለልጁ የሚያደርገውን የሓላፊነት ሽግግር ዝግጅትና ጊዜ ሊጠይቅ ይችላል። የሚሴና የኢያሱ የመሪነት ቅብብሎሽም ለዚህ አባባል ዓይነተኛ ምሳሌ ነው። “ንገር ግን እኛ ሰዎች ታሪክ እንማራለን እንጂ ከታሪክ አንማርም!” … መሪነት ማለት ሰዎች በፈቃደኝነት ለአንድ ዓላማና ግብ ለማሰለፍና የማግባባት ችሎታ ያላቸው ማለት ነው።“
ኅይልና ሥልጣን
የመሪነትን ተግባር በአግባቡ ለማወቅ ኅይልና ሥልጣን (Power & Authority) የተባሉትን ጽንስ–ሐሳቦች መገንዘብ ያስፈልጋል።
ኅይል (Power)
አንድ ሰው ሌሎችን ለመምራት ያለው ዕምቅ ችሎታ የሚታወቅበት (የሚገለጽበት) ሲሆን ዋና ዋና ዘዴዎቹም፦
- በሕግ መሠረት በሚሰጡ ሓላፊነቶች
- ግለሰቡ ለመግባባት የሚጠቀምባቸው ዘዴዎች
- ለማስፈጸም በሚፈጥራቸው ጤናማ የሆኑ ጫናዎች
- ከችሎታው፣ ከልምዱና ከእውቀቱ በሚመነጩ ኹኔታዎች
የመሳሰሉትን የሚያጠቃለል ነው።
ለ. ሥልጣን (Authority)
አመራር ለመስጠትና በሥሩ ባሉት መሠረታዊ ሀብቶች ለመጠቀም የሚሰጥ ሕጋዊ መብት ማለት ነው።
ስለሆነም አንድ መሪ ተገቢውን የመሪነት ሚና ለመጫወት ኅይልና ሥልጣንን በየዐውዳቸው መጠቀም ይጠበቅበታል ማለት ነው። ሐዋርያው እንዳለው የእግዚአብሔርን ቤት እንዴት እንደምታስተዳድር ታውቅ ዘንድ እጽፍልሀአለሁ፤ ቤተ ክርስቲያኒቱ የእውነት ዓምድና መሠረት የሕያው እግዚአብሔር ቤት ናት። (1. ጢሞ. 3፥15)
የቤተ ክርስቲያን ኅልውና በሥራ የሚገለጥ ሃይማኖት ነው፤ የሃይማኖት ፍሬም እውነተኛ የአስተዳደር ፍቅር ነው። በቤተ ክርስቲያን እግዚአብሔርንና ሰውን ሊያስደስት የሚችለው ሥልጣንና ገንዘብ አይደለም። ሊሆን የሚገባውን ፍሬ ሊያፈራ የሚችለው በእውነት በተመደበበት የሓላፊነት ሥራ በታማኝነት ሲያገለግል ብቻ ነው።
ውጤታማ የኾነ አመራር መስጠት የሚቻለው የሰዎችን ፈቃደኝነት በተመረኮዘ ኹኔታ በመግባባት በመሆኑ ለማግባባት ደግሞ ጤናማ ግንኙነትን መፍጠር ግዴታ ይሆናል።
ጤናማ ግንኙነት ለመፍጠር መሪዎች ምን ማድረግ አለባቸው?
- ኅይልና ሥልጣናቸውን በተገቢው አኳኋን መጠቀም፣
- ተከታዮቻቸውን ከከፍተኛ ደረጃ ማብቃትና ማዘጋጀት፣
- በተከታዮቻቸው ዘንድ ያላቸውን ተቀባይነት የበለጠ ማሳደግና ማስፋፋት፣
- ከሥነ–ምግባር ውጭ የሆኑ የማግባባት ዘዴዎችን አለመጠቀም፣
- መነሻቸውን ከሰዎች መልካም ነገር እንደሚጠበቅ አድርጎ ግንኙነት መፍጠር (Positive expectation)፣
- ራስን ለለውጥና ለአዳዲስ ነገር ዝግጁ አድርጎ መጠበቅ፣
- የሕዝብን አስተያየት ለአመራር ተግባር ሊኖረው የሚገባውን ድርሻ መገንዘብ፣
- ከሰዎች ጋር ለሚኖር ግንኙነት ተገቢውን ዝግጅት ማድረግና ውጤታማና ማራኪ
- በሆነ አቀራረብ ለመቅረብ መጣር
- ከስሜታዊ እንቅስቃሴዎች መቆጠብ እንደሚገባ ያስረዳል።
መሪና ትሕትና
ለመንፈሳዊ መሪ ትሕትና የማዕር ልዩ ምልክት ነው ወይም ኒሻኑ ነው። ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ደቀ መዛሙርቱን ከመታበይ አሮጌ እርሾ ይርቁ ዘንድ ይመክራቸው ነበር። ከዚህ ይልቅ ትሕትናን የተላበሱ ባርያን ይመስሉ ዘንድ ያሳስባቸው ነበር (ማቴ. 20፥25)። ትሕትና፡ በፖለቲካው እና በንግዱ ዓለም ጥቂት ብቻ አድናቆት የሚቸረው ጉዳይ ነው። ይህ ግን ትክክለኛ አይደለም። አንድ መንፈሳዊ መሪ ከእይታ ስውር የኾነውን እና መሥዋዕትነትን የሚጠይቀውን አገልግሎት የሚመርጥ፣ ከሌሎች ልቆ ለመገኘት እና በሁሉ ላይ የሠለጠነ ጌታ መኾኑን ለማረጋገጥ ሲል ራሱን ከመጠን በላይ የሚያስታጅረውንና ልታይ ልታይ የሚለውን ሰው ሊመስል አይገባውም።
መንፈሳዊ መሪ እና ትዕግሥት
መንፈሳዊ መሪ ጤና የኾነ ትዕግሥትን ገንዘቡ ሊያደርግ ይገባዋል። ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅም ትዕግሥትን “የመልካም ሥራ ሁሉ እናት ናት” ያላታል። ሁልጊዜ ትዕግሥትን ስናስብ አንዴ ተከውኖ ድጋሚ የማይፈጸም አድርገን ልንቆጥረው አይገባንም። ትዕግሥተኛ ሰው ግማሽ በማንቀላፋትና እንደ መሩት እንደሚመራ ሰዎ አድርገን እንመስለዋለን። ነገር ግን እንዲህ ዐይነት ትርጉም መጽሐፍ ቅዱሳዊ ማስተካከያ ሊደረግበት ይገባል። (2ጴጥ. 1፥6)
ቃሉ ፈጽሞ እጅን አጣጥፎና ነገሮችን ዝም ብሎ ለመቀበል መንፈስ ታስቦ መተርጎም የለበትም። ይልቁኑ ሁሌም አሸናፊ ኾኖ ለመዝለቅ መከራን ተቋቁሞ የማስፈን ትርጉም የሚሰጠን ቃል ንው።
ይህ አንድ ክርስቲያን በቆራጥነትና በእልህ በዚህ ዓለም የሚገጥሙትን የኑሮ ፈተናዎችን ትቋቁሞ የሚያልፍበት፣ እጅግ አስቸጋሪ ሁኔታዎችን በመለወጥ ደስታ ወዳለበት ከፍታ እንዲደርሱ የሚያግዝ መሳሪያ ነው።
ነገሮችን ተቋቁሞ በሰው ያልተደፈሩትን ሰብሮ ለመግባት፤ ጽናትን እና ድል አድራጊነትን ሊያሰጥ፤ አቅምን ሊፈጥር የምችል እና የማይታየውን በመናፈቅ በደስታ ለመቀበል የሚናፍቅ ነው።
ትዕግሥት በማኅበራዊ ቁርኝታችን በእጅጉ የሚፈተን ነው። ቅዱስ ጳውሎስ ማርቆስ ከሚባለው ዮሐንስ ጋር ባደረገው ክርክር ትዕግሥቱ አልቆ ነበር።
መንፈሳዊ መሪ ትዕግሥትን ከተከታዮች በመራቅ ሊገልጸው አይገባም። ይህ እንዲያዝኑ ያደርጋቸዋል። ነገር ግን የመሪነቱን ቦታ ሳይለቅ ከጎናቸው ሲቆም ራሱን ብቻ ከመመልከት እና ከመስማት በመቆጠብ ሊመላለስ ይገባዋል። ለተከታዮች ማሰብን አጠንክሮ መያዝ ካልቻለ ራሱን በጽናት ማቆም የሚቻለው የለም። “እኛ ኅይለኞች የሆንን የደካሞችን ድካም እንድንሸከም ራሳችንን ደስ እንድናሰኝ ይጋብዘናል፤” (ሮሜ. 15፥1)።
አንድ ሰው የሰውን ድካም ሊታገሥ የማይችል ከኾነ መሪ ለመኾን የተገባ አይደለም። የእኛ ጥንካሬ የሚለካው ከፊታችን ቀድመው በሚሮጡት እና በእኛና በእነርሱ መካከል ባለው ርቀት መጠን ሳይሆን ከእኛ አጠገብ ባሉት ጎን ፈጥነን በመሄዳችን ስለእነርሱ ስንል ቀስ ብለን ርምጃችንን በእነርሱ ፍጥነት ያደረግን ከኾነ ነው። የእኛ እርዳታ እነርሱን ከውድቀታቸው የሚያነሣ፣ መንገዱን ያሳየናቸውና ያሻገርናቸው እንደ ኾነ ብቻ ነው።
ይህ መነበብ ያለበት መጽሐፍ ባጠቃላይ የሚከተሉትን ጉዳዮች ይመለከታል፦
- ምዕራፍ አንድ፡ መሪ እና አመራሩ
- ምዕራፍ ሁለት፡ የተፈጥሮአዊ እና መንፈሳዊ መሪነት እይታዎች
- ምዕራፍ ሦስት፡ የመሪነት አእምሮ መመዘኛዎች
- ምዕራፍ አራት፡ የመሪነት ዐበይት ተምሳሌታዊ ምክሮች
- ምዕራፍ አምስት፡ የአለመግባባት ዐበይት ምክንያቶች ምንድን ናቸው?
- ምዕራፍ ስድስት፡ ሙስና እና መሪነት
- ምዕራፍ ሰባት፡ ጽናትና መሪ
- ምዕራፍ ስምንት፡ ብልህነት እና ዲፕሎማሲ
- ምዕራፍ ዘጠኝ፡ ከሁሉ በላይ የሆነው ጉዳይ የመሪዎች መንፈሳዊነት
- ምዕራፍ ዐሥር፡ መሪ እና ጊዜ
- ምዕራፍ ዐሥራ አንድ፡ የመሪነት ክህሎት ማሳደግ