ለሕይወትህ አምልጥ
Posted by addisethiopia / አዲስ ኢትዮጵያ on January 22, 2012
አንድ በጣም ብርቱ ውሻ ስላለው የሩጫ ብቃት እያነሳ በሌሎች ውሾች ላይ ጉራውን ይነዛባቸው ነበር። ከዕለታት አንድ ቀን ታዲያ አንዲት ጥንቸል ሊያድን ወሻው ሊይዛት ስላልቻለ አመለጠችው። ሌሎቹ ውሾችም እንዲህ እያሉ ትሳለቁበት፦ “የሩጫ ኃይልህ ወዴት ደረሰ? እንዴት አንዲት ደካማ ጥንቸል በሩጫ ልትቀድምህና ልታመልጥህ ቻለች?”
ውሻው ለጥቂት ደቂቃዎች ዝም ብሎ ከቆየ በኋላ “ጥንቸሏ የምትሮጠው ሕይወቷን ለማዳን እኔ የምሮጠው ግን እራቴን ለማግኘት መሆኑን አትርሱ!” አላቸው።
ጥንቸሏ ውሻውን ልትቀድመው የቻለችው ሕይወቷን ለማዳን ስለምትሮጥ ነበር። ይሁን እንጂ ውሻው ይሮጥ የነበረው ጥንቸሊቷን ለማደንና ለመብላት ነበር። ለሕይወታችን ስንሮጥ ጠላታችን እንዳይዘንና እንዳይበላን ስለምንሮጥ ለየት ያለ ችሎታ ነው የሚኖረን።
ኃጢአት ነፍሶቻችሁን የሚአጎድልና ዘላለማዊ ሕይወታችሁን የሚያጠፋ መሆኑን ከተረዳችሁ ማምለጥ ኃይልና ድፍረት ነው።
ውሻ፡
ው፡ ው፡ ው፡ ው፡ ው፡
እግዚአብሔር ይመስገን የላይኛው ጌታ
እኔን የፈጠረኝ እንዳልንገላታ።
ውሻ በመባሌ ጥቂት ቅር ይለኛል፡
ባለሟል መሆኔን ማን ያስብልኛል።
ከፍጥረቶች ሁሉ ውሻ ርኩስ መባሌ፡
አልታወቀ ይሆን ከልፍኝ ውስጥ መዋሌ?
ሌሊት እየጮሁኝ ሌባ ሳላስቀርብ፡
አድራለሁ እስከጧት ተቀጥሬ ለዘብ።
ቀንም በሰንሰለት ታስሬ በፍንጅ፡
ጠላት አላስደርስ ከጌታዬ ደጅ፡
ላደን የወጣ እንዲሁ ጌታዬ ይዞኝ፡
እንኳን ያሳየኝን ወፍ አያመልጠኝ።
እንዲህ ስላልኳችሁ ቅዱስ ነኝ አላልኩም፡
ቅዱስንም ነገር ለኔ ስጡ አልልም፡
ተወስኗልና ጥንቱን በመጽሐፍም።
ከበላሁ ከጠጣሁ ምንም ብሆን ውሻ፡
ውለታ መላሽ ነኝ ለጌታዬ ጋሻ፡
ከቶ አልደለለም በባዕድ ሰው ጉርሻ።
በውሻነቴ እንዲሁ ስሜን የጠላችሁ፡
ችሎ ማደር ይሁን ለናንት ይመቻችሁ።
ሲዋሹም እንደሆን ወይም ሲደልሉ፡
ሲተረት ሰምቼ ደስ ብሎኛል ቃሉ፡
“ለሰው ልጅ ሲያበሉ ለውሻ ልጅ ያብሉ፡“
እስከዚህ ድረስ ነው የኔ ሙያ ሁሉ፡
ጌታዬን መውደዴ ታውቋል ባለም ሙሉ።
ደግሞ ልንገራችሁ የሰማሁትን ጉድ፡
አያድርም ይላሉ ቅቤ በውሻ ሆድ።
ባያየው ነው እንጂ ሆዱን ባይመረምር፡
ቅቤ አቅልጥ ያልሆነ አይገኝ ከፍጡር።
___________________________
Leave a Reply