ጀግና ኢትዮጵያውያን – አፄ ዮሐንስ
Posted by addisethiopia / አዲስ ኢትዮጵያ on July 10, 2011
‘ዮሐንስ‘ – በማሞ ውድነህ፡ ፲፱፻፹፭ ዓ.ም
የግብጽ ወታደሮች በምስራቅ ግንባር ሙሉ በሙሉ መደምሰሳቸው የሰሙት የግብጹ ሼህ ገዢ፡ አማካሪያቸው የነበረውን አሜሪካዊ ጀኔራል ሎሪንግ ጠርተው ምክር ይቀበሉ ጀመር፡ በወቅቱም ከግብጽ ጋር የተሰለፉ ኢትዮጽያውያን መኮንኖች ሸሆች አብረዋቸው ነበሩ። እንደነ ደጃጅማች ሚካኤል የመሳሰሉት።
“በኛ በአሜሪካኖች ዘንድ አንድ ምሳሌ አለ። አንድ ጊዜ ሞክረህ ቢከሽፍብህ ሁለተኛ ሞክር፡ ሁለተኛውም ባይሳካልህ ሦስተኛ ሞክር፡ ሦስተኛውም ካልተሳካልህ ደግሞ ሞክር፡ ዕድሜህን ሙሉ ሞክር፡ ሞክር” ይላል። ታላቂቱ ግብጽ ሁለት ሺህ አምስት መቶ ወታደሮች ባልሠለጠኑ ሕዝቦች ቢያልቁባትም፡ ከሰላሣ ሺህ በላይ የሚሆን ወታደር ያላት ናትና እንድገና ይሞክር” ብሎ ደነፋ።
በዚህ አነጋገሩ የግብጹ ገዢ ከዲብ እስማኤል የተደሰተበት መሆኑን በአካኋኑ ጭምር ሲያረጋግጥ የተመለከተው ልጁ ሑሴን እስማኤልም ተነሣና፡ “በቱርኮች እግር ተተክተን ግብጽን እጅግ የላቀች ሰፊ ግዛት ያላት አገር ለማድረግ ታጥቀን ተነሥተናል። ስለዚህ በአንድ ያልሠለጠነ ንጉሥ መዋረዳችንን ልንታገሠው የማይገባን ጉዳይ ስለሆነ ዛሬውኑ እንዝመት” ብሎ ለአባቱም ወታደራዊ ንቃቱን አሳይቶ ተቀመጠ።
ፓሻም፡ “የደረሰብን ውርደት መራራ ቢሆንም ዛሬውኑ መበቀል አለብንና በፍጥነት ወደ አበሾች አገርን እንገስግስ” አለ።
“ይህን ውርደት የግብጽ ሕዝብ ከመስማቱ በፊት ራሴ ዘምቼ እበቀልለታለሁ” አለ ከዲብ እስማኤል።
“ስማኝ ታላቁ አባቴ፡ ምንም እንኳን ከታላቁ ክንድህ አበሾች የማያመልጡም ቢሆኑ የአንተ መዝመት ከእነርሱ ታላቅ ክብራቸው ነውና እኔ እዘምታለሁ…” ብሎ ሑሴን እስማኤልም ፎከረ።
ከዲብ እስማኤል ፍሬ ነገሩን ከልጁ ሑሴን አንድበት ቀበል አደረገና፡
“ጠላትህን አትናቀው” ተብሏልና ከእንግዲህ ወዲያ አበሾችን አንንቅም፡ ራሴ እዘምትባቸዋለሁ” ብሎ ነገሩን አጠነከረው።
ከዲብ ቀጠል አረገና፡ “ለመሆኑ ዮሐንስን የሚረዳ የውጭ መንግሥት ይኖር ይሆን?” ብሎ ጄነራል ሎሪንግን ጠየቀው።
“ምናልባት ፈረንሣዮች ይረዱ ይሆናል” አለ ሎሪንግ።
“ፈረንሣዮችማ ዮሐንስ በአገሩ የሚኖሩትን ሚሲዮናውያን ዜጎቻችንን አስቸግሮብናልና ጠበቅ ያለ ርምጃ ውሰዱበት። ጳጳስም አትላኩለት” እያሉ ሲወተውቱኝ አልነበር? እንዴት ይረዱታል?” አለ ከዲቡ።
“ምናልባት እንግሊዞችስ?” አለና ሎሪንግ ጠየቀ።
“ለእንግሊዞችም ቢሆን የምንሻላቸው እኛ ነን። ቀይ ባሕርንና የአባይን ወንዝ ብንይዝላቸው ይደሰቱበታል እንጂ ቅር አይሰኙም። በኛስ ላይ ዐይኖቻቸውን እንደ ጣሉብን ያሉት እነርሱው አይደሉም? በኛ መሥዋዕትነት ለምለምና አስፈላጊ የሆነች አገር ብንይዝ ቅር ይላቸው ይመስልሃል?” አለ ከዲብ ሎሪንግን እያስተዋለው።
“እንግዲያውማ?” ብሎ ሊሪንግ ከዲቡንና ከዳተኛ ኢትዮጵያውያን መኮንኖቹን ተመልክቶ “እንግዲያውማ ጀርመኖችም በአበሻ ጉዳይ እጅግም የሚያስቡበት አይመስሉም። የሩስያው ንጉሥም ስለ አበሻ አገርና መንግሥት ሰፋ ያለ ጥናት ያደረጉ አይመስሉምና ለማንኛውም የሚያዋጣው በፍጥነት መዝመቱ ይመስለኛል” አለ።
በዚሁ ውሳኔና በወጣው ስልት መሠረትም ግብጽ ለሁለተኛ ጊዜ በሐሰን እስማኤል ጠቅላይ አዛዥነት በራቲቮ ፓሻና በጀነራል ሎሪንግ አዝማችነት ከዐሥራ ሦስት ሺህ በላይ የሆነ ጦር ወደ ኢትዮጵያ አዘመተች። በአዋጊነታቸው እምነት የተጣለባቸው ስድስት አሜሪካውያን ከፍተኛ መኮንኖችና በርካታ የመስመር መኮንኖችም ተደለደሉ።
አንዳንዶቹ የመስመር መኮንኖች፡ “ግብጽ የያዘችውን የራስዋን ግዛት ምን ሠራችበትና ነው? የአበሻን አገር እይዛለሁ ብላ የምትዋጋው? ትላንት ጉንደት ላይ የደረሰባት ሽንፈት መች አነሰና ነው ዛሬ ደግሞ ቁጥሩ ወደ ሁለት መቶ ሺህ ከሚጠጋ ሠራዊት ጋር ጦርነት ግጠሙ ብላ የላከችን?” እያሉ ያነሡትን ጥያቄ ጦሩ የሚደግፈው ሆነ።
ምንም እንኳን ከዲብ እስማኤል ጥብቅ ማስጠንቀቂያ ቢልክም በመኮንኖቹ መካከል የተነሣውን ውዝግብና ጦሩም ያነሣውን ጥያቄ ሊሽረው ባለመቻሉ አዛዦች ከውጊያ ስልት፡ ከሥነ ሥርዓትና ከተዋጊነት ሞራል እንደ ተራራቁ ከምጽዋ ወደ ደጋው ሐማሴን የሚወጡበትን የጉዞ እቅድ ነደፉ።
ግብጾች ዘንድ ሰርጎ በመግባት ይህ ነው የማይባል የስለላ አገልግሎት ለጀግናው ራስ አሉላ ብሎም ለአፄ ዮሐንስ ሲያበረክት የነበረው ቅኑ ኢትዮጵያዊ ገብረ መስቀልም በወጥቤትነቱና በአሽከርነቱ ከግብጽ ጦር ጋር ሐማሴን ገብቶ የደጃዝማች ወልደ ሚካኤልንና አብረዋቸው ወደ ግብጽ ጦር የገቡትን መኳንንትና ሼሆች ዝርዝር ለሊጋባ አሉላ አስተላለፈ። የሐማሴንን መያዝና የወልደ ሚካኤልንም መክዳት አጼ ዮሐንስ እንደሰሙ፡ ሁለተኛውንና የመጨረሻውን የመከላከል ዝግጅታቸውን ጀመሩ፡ ኢትዮጵያዊ ሁሉ እንዲከተላቸው የመጨረሻውን ዐዋጅ ዐወጁ።
“ዐዋጅ ዐዋጅ ዐዋጅ ስማ ብለውሃል ስማ፤
በበጌምድር፡ በወሎ፡ በጎጃም፡ በሐማሴን፡ በትግራይ፡ በሸዋ ፡ በዳር አገር ያለህ ያገሬ ሰው ሁሉ ስማ፤ የእርስ በርሳችንን መናናቅና መጋጨት ጠላት ዐውቆ በመካከላችን ገብቶ አገር ለመውረር ቢመጣ ጀግናውን ሠራዊቴን አሰልፌ ጉንደት ላይ ብገጥመው ድል ሆነ። ብትንትኑ ወጣ፤ ግን ምን ይሆናል፤ በቃኝ አላለምና እንደገና ደግሞ መጣ። የግብጡ ንጉሥ ደሜን እመልሳለሁ ብሎ ርስትህን፡ ሚስትህን፡ አገርህን፡ ቤት ንብረትህን ሊቀማ እንደገና ጦሩን ልኮብናል።
እኔ ዮሐንስ እንደሆንኩ ሐሳቤም፡ ነፍሴም፡ ሃይማኖቴም አንዲት ናት፡ የሀገሬን መደፈር የሕዝቤን መዋረድ በሕይወቴ ቁሜ አላይም፤ አልሰማም፡ የሚንቁኝንና አንበገርልህም የሚሉኝን እገጥማለሁ፤ ብዬ ጦሬን ወደ ወንድሞቼ አላዞርም። ወደ መጣብኝ ጠላት ዘምቻለሁና ክተት። ስንቅህን ስንቅ፡ ጋሻ ጦርህን አንግበህ ተከተለኝ፡ የመጣው ጠላት የኔ ብቻ ጠላት መስሎህ ዝም ብትል አገርህን ማስወሰድህን ዕወቅ። ይህን ቃል ሰምተህ እንዳልሰማህ ሆነህ ብትቀር ሥጋህን ለአራዊት፡ ነፍስህን ለገሀነም እሳት ዳርጌዋለሁ።“
አባትህና ንጉሠ ነገሥትህ
ዮሐንስ ንጉሠ ጽዮን።
ቀሳውስቱም በጳጳሱ በአቡነ አትናቴዎስ ስም አስመስለው ቀጥሎ ያለውን ቃል አሳወጁ።
“ሃይማኖትህን ሊያጠፋ፡ ርስትህንና ሚስትህን ሊቀማ የመጣውን የግብጥ ጦር ባትወጋ እስከ ሰባት ትውልድህ ድረስ ርጉም ሁን። የንጉሠ ነገሥትህን የዮሐንስን ዐዋጅ እንዳትጥስ ገዝቼሃለሁ።“
Continue reading… AtseYohannesV
የማሞ ውድነህ ገጸ በረከት « AddisEthiopia Weblog said
[…] ለምሳሌ፤“ዮሐንስ” በሚለው መጽሐፋቸው የሚከተለውን ማሳሰቢያ እናነባለን፡ […]